Friday, July 12, 2013

የደኅንነት ሠራተኞች ኃላፊነታቸውን ሲወጡ ለሚወስዱት ዕርምጃ በሕግ አይጠየቁም የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት በሚኒስቴር ደረጃ ሊቋቋም

JUN 26 2013

-የደኅንነት ሠራተኞች ኃላፊነታቸውን ሲወጡ ለሚወስዱት ዕርምጃ በሕግ አይጠየቁም
-ማንኛውም ሰው መረጃ መጠየቁንና መስጠቱን በሚስጥር የመያዝ ግዴታ አለበት
ብሔራዊ የመረጃና ደኅንነት አገልግሎት ተቋምን በሚኒስቴር ደረጃ እንደገና የሚያቋቁም ረቂቅ አዋጅ ለፓርላማ ቀረበ፡፡
ብሔራዊ የመረጃና ደኅንነት አገልግሎት በ1987 ዓ.ም. በወጣ አዋጅ የተቋቋመ ሲሆን፣ ከዚህ በኋላ በርካታ አገራዊ፣ አካባቢያዊ፣ አኅጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ሁኔታዎች ላይ ለውጦች መታየታቸውና እነዚህ ለውጦች በኢትዮጵያ ደኅንነት ላይ ያላቸውን ፋይዳ ባገናዘበ ሁኔታ በተቋሙ ላይ ለውጥ መፍጠር በማስፈለጉ፣ ማሻሻያው እንዲደረግ መወሰኑን የጠቅላይ ሚኒስቴር ጽሕፈት ቤት አባሪ ያደረገው መግለጫ ያስረዳል፡፡
በዚህም መሠረት የአገር መከላከያን፣ የአገር ደኅንነትንና ሉዓላዊነትን የማስጠበቅ ሥልጣንና ተግባር የፌዴራል መንግሥት እንደመሆኑ መጠን፣ የመረጃና ደኅንነት አገልግሎት በአገር ደረጃ የሚዋቀር ብቸኛ ተቋም ሆኖ ክልሎች መሰል ተቋም ሊኖሯቸው እንደማይችል በማመልከት አዋጁ ተረቋል፡፡
አገልግሎቱ ካለበት ሕገ መንግሥታዊና አገራዊ ኃላፊነት እንዲሁም ካለው ሰፊ ሥልጣንና ተግባር አንፃር በሚኒስቴር ደረጃ እንዲዋቀር በረቂቅ አዋጁ ተካቷል፡፡
ተቋሙ ለሕዝብ ጥቅም አስፈላጊ ነው ብሎ ሲያምን የሒሳብ መዛግብትና ሌሎች የሥራ መረጃዎችን እጅግ ብርቱ ሚስጥር ብሎ በመሰየም ለሌሎች አካላት (የፈዴራል ኦዲተርንም ቢሆን) ሊከለክል እንደሚችል በረቂቁ ላይ ተካቷል፡፡
ይህ ሥልጣን ቢኖረውም በውስጥ ኦዲተርና ለጠቅላይ ሚኒስትሩ በሚቀርብ ሪፖርት መነሻነት ክትትልና ቁጥጥር ስለሚደረግበት፣ የተጠያቂነት ሥርዓቱ ላይ ጥያቄ የማያጭር መሆኑን የጠቅላይ ሚኒስቴር ጽሕፈት ቤት አባሪ መግለጫ ያስረዳል፡፡
በመሆኑም ተቋሙ ከውጭ አገር የሚያስገባቸውን የመረጃ ደኅንነት መሣሪያዎች ወይም ዕቃዎች ለጉምሩክ ሳይገለጹ እንዲገቡ ማድረግ ሲችል፣ ወደ ውጭ የሚላኩ ተመሳሳይ መሣሪያዎች ሚስጥራዊ ባህሪያቸው እንደተጠበቀ እንዲንቀሳቀሱ አዋጁ ይፈቅዳል፡፡
የተቋሙ የደኅንነት ሠራተኞች ማንነትና የሀብት መጠን ሚስጥራዊ በሆነ ሁኔታ እንዲጠበቅ የማድረግ ኃላፊነትም በረቂቁ ተካቷል፡፡ በተጨማሪም ተቋሙ ከአገር ውስጥ የሕግ አስከባሪ አካላት ጋር በፀጥታ ዙሪያ በቅንጅት እንዲሠራ ትብብሩና መደጋገፉ በአጋር አካላት በጐ ፈቃደኝነት ላይ የተሠረተ ሳይሆን፣ ግዴታን የጣለ ረቂቅ አንቀጽ ተካቷል፡፡
የአቪዬሽን ደኅንነትን በበላይነት የመምራት፣ ብሔራዊ የመታወቂያ ካርድ የመስጠት ሥራን በበላይነት የመምራት፣ እንዲሁም ለግል ጥበቃ ድርጅቶችና ሠራተኞች የማረጋገጫ ሠርተፊኬት የመስጠት ኃላፊነቶች ተሰጥተውታል፡፡
የተቋሙ የደኅንነት ሠራተኛ ኃላፊነቱን በአግባቡ በሚወጣበት ወቅት በነበሩ አስገዳጅ ሁኔታዎች ለሚወስደው ዕርምጃ በወንጀልም ሆነ በፍትሐ ብሔር ወንጀል እንደማይጠየቅ ረቂቁ ያስረዳል፡፡
የደኅንነት ሠራተኞች በሥራ ላይም ሆነ ከተሰናበቱ በኋላ በሥራ አጋጣሚ የሚያውቋቸውን ሚስጥሮች የመጠበቅ ግዴታ የተጣለባቸው ሲሆን፣ ማንኛውም ሰው በተቋሙ መረጃ ተጠይቆና ሰጥቶ ስለመሆኑ በቸልተኝነት እንኳን ለሌሎች ቢያሳውቅ በወንጀል እንደሚጠየቅ ረቂቅ አዋጁ ይገልጻል፡፡
በተጨማሪም የተቋሙ ሠራተኛ ያልሆነ ግለሰብ በተቋሙ፣ በኃላፊው ወይም በደኅንነት ሠራተኞች ስም በቃል ወይም በድርጊት ለማታለልና ለማስመሰል የሞከረና የተቋሙን ተግባር ያወከ ግለሰብ፣ በወንጀል ሕግ ድንጋጌዎች እንደሚቀጣ በረቂቁ ተካቷል፡፡ ረቂቁ ለዝርዝር ዕይታ ለሕግና ፍትሕ አስተዳደር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ በዋናነት ተመርቷል፡፡
ethiopian reporter

No comments:

Post a Comment