Monday, November 2, 2015

የፌዴራል ዓቃቤ ሕግ አራት የአምቦ ከተማ የኦሮሞ ወጣቶችን በኦነግነት ከሰሰ


(Oromedia) — የፌዴራል ዓቃቤ ሕግ አራት በኦሮሚያ ምዕራብ ሸዋ ዞን የአምቦ ከተማ የኦሮሞ ወጣቶችን በኦነግነት በመወንጀል ጥቅምት 17 ቀን 2008 ዓ.ም. ክስ መሠረተባቸው፡፡
ተጠርጣሪዎቹ የኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ) አባል በመሆንና ተልዕኮውን በመቀበል፣ በአገር ውስጥና በውጭ አገሮች ከሚገኙ አባላቱ ጋር በስልክ በመገናኘት፣ በከተማው ሰላማዊ ነዋሪዎችና በመንግሥት ተቋማት ላይ ጉዳት ለማድረስ በመንቀሳቀስ፣ አንድ የመከላከያ ሠራዊት አባል በመግደልና በሌሎች የመንግሥት አመራሮችና ነዋሪዎች ላይ ከባድ የአካል ጉዳት በማድረስ በማለት፣ የፌዴራል ዓቃቤ ሕግ ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 19ኛ ወንጀል ችሎት ያቀረበው ክስ ያስረዳል፡፡
ተከሳሾቹ ቀጄላ ገላና ቅጽል ስሙ ሙረታ ሰባ፣ አብደታ ዶላንሳ ቅጽል ስሙ ዴኔዲዳ፣ ሰብኬር በቀለ ቅጽል ስሙ ከዩ ድጋና ኡርጌሶ ደመና ቅጽል ስሙ አብደታ ደመና የሚባሉ ናቸው፡፡ ከ2006 ዓ.ም. ጀምሮ ካልተያዙ ግብረ አበሮቻቸው ጋር በመሆን በህቡዕ ስብሰባ በማድረግ፣ በሚያዝያ ወር 2007 ዓ.ም. ‹‹ኦጋፋ ኢጌ ጉማ ኦሮሞ›› የሚባል የህዋስ ቡድን ስያሜ ማውጣታቸውን ዓቃቤ ሕግ በክሱ ጠቅሷል፡፡
ተከሳሾቹ የኦነግን የፖለቲካ ዓላማን ለማራመድ በመስማማት በተቀበሉት ትዕዛዝ መሠረት፣ በአምቦ ከተማ በቀበሌ 03 ነዋሪና የቀበሌው ምክትል ሊቀመንበርን በአራት ጥይት መትተው ማቁሰላቸውንና አንድ ዓይናቸውን ማጥፋታቸውን፣ በምዕራብ ሸዋ ፖሊስ መምርያ ግቢ ውስጥ ቦምብ በመወርወር በጽሕፈት ቤቱ ላይ ጉዳት ማድረሳቸውን፣ የሆሚች አሙኒሽን ኢንጂነሪንግ ኢንዱስትሪ ንብረት በሆነው ቢሾፍቱ የሠራተኞች ሰርቪስ ላይ ቦምብ በመወርወር 213,000 ብር በሚገመት ንብረት ላይ ጉዳት ማድረሳቸውን፣ በአምቦ ቴክኒክና ሙያ ኮሌጅ ይማር የነበረውን የመከላከያ ሠራዊት አባል የነበረው ዳርጌ ኡርጌሳን መግደላቸውንና ሌሎች የወንጀል ተግባራትን መፈጸማቸውን ዓቃቤ ሕግ በክሱ ዘርዝሮ አቅርቧል፡፡
ኡርጌሳ ደመና የተባለው ተከሳሽ የኦነግ አባል ሆኖ ሲንቀሳቀስ ከየካቲት ወር 2006 ዓ.ም. ጀምሮ ሞቲ ሞቱማ በተባለ ግለሰብ አማካይነት፣ በውጭ ለሚገኙ የኦነግ መገናኛ ብዙኃን መረጃ ለማቀበል ተስማምቶ በተለያዩ የሚስጥር ስሞችና በተለያዩ ስልኮች በመጠቀም፣ አምቦ ከተማ ውስጥ ስለሚገኙ የኦነግ አባላት ህዋስ አደረጃጀትና ምልመላ መረጃ ሲያስተላልፍ እንደነበር ክሱ ያስረዳል፡፡
ተከሳሾቹ የኦነግን ተልዕኮ ተቀብለው በህቡዕ በህዋስ ተደራጅተው በአምቦ ከተማ ሰላማዊ ነዋሪዎችና በመንግሥት ተቋማት ላይ ጥቃት በመፈጸማቸው፣ የመከላከያ ሠራዊት አባልን በመግደላቸው፣ ከባድ የአካል ጉዳት በማድረሳቸውና ሌሎች ወንጀሎችን ለመፈጸም ሲንቀሳቀሱ በመያዛቸው፣ በፀረ ሽብርተኝነት አዋጅ ቁጥር 652/2001 አንቀጽ 3(1እና4) ላይ የተደነገገውን ተላልፈዋል በማለት ዓቃቤ ሕግ በዋና ወንጀል ተካፋይ መሆናቸውን በክሱ አስረድቷል፡፡
ፍርድ ቤቱ መቃወሚያ ካለ ለመቀበል ለጥቅምት 23 ቀን 2008 ዓ.ም. ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

No comments:

Post a Comment