Tuesday, April 2, 2013

የሌንጮ ለታ አዲሱ ትግል – እንዴት?

ስለ ኦነግ ሲነሳ አብዛኞች በመገረም የሚናገሩትና ሚዛን የሚደፋው አስተያየት የሚሰነዘረው በድርጅቱ መከፋፈልና መበጣጠስ ሳይሆን ተለያይተውም አስመራን የሙጥኝ ያሉበት ምክንያት ነው። ኢህአዴግ ህጻን እያለ ሻዕቢያ እንዳሻው ይነዳው እንደነበር የሚያስታውሱ አስተያየት ሰጪዎች ከሽግግር መንግስት ምስረታ በኋላ ኦነግ አገር ለቆ እንዲወጣ መንገዱን የጠረገው ሻዕቢያ መሆኑንን በቁጭት ይናገራሉ።
ኢህአዴግ ለስልጣን አዲስ በሆነበት የጨቅላነት ዘመኑ፣ ኦነግ በታሪኩ ያልነበረውን ሰራዊት በመገንባት አስጨንቆት እንደነበር በመጠቆም በወቅቱ አስተያየት የሰጡ ኢህአዴግ በተለይም መለስ በሻዕቢያ በኩል ኦነግን ለመታረቅ አቅርበውት የነበረውን የሽምግልና ጥያቄ ኦነግ እንዳይቀበል ሰሚ ባያገኙም በአጽዕኖት ምክራቸውን ሰጥተው ነበር።
በኦነግ ታጣቂ ሃይሎችና በኢህአዴግ ሰራዊት መካከል እኩል ሊባል በሚችል ደረጃ የጡንቻ መፈታተን ነበር። ደርግ ሲበታተን ኦነግን የተቀላቀሉ የቀድሞው የኢትዮጵያ ሰራዊት አካላት ወያኔን የማዳፋት አቅሙ ነበራቸው። በወቅቱ የንስር ያህል ጉልበትና ሃይል ቢኖራቸውም ራሳቸውን ጫጩት አድርገው ተመለከቱ። አዲስ አበባ ሲገቡ የነበራቸውን የህዝብ ድጋፍ አራግፈው ጣሉት። በስሜት እየተነዱ ከሚወዷቸው ሁሉ ተቀያየሙ። ህወሃት አጋጣሚውን ለቅስቀሳና ለስም ማቆሸሻ ሰራበት። በስተመጨረሻ ኦነግ ሃይሉንና አቅሙን ዘንግቶ በአመራር ችግርና በአቋም ሸውራራነት ሃይሉን በሙሉ ወደ ካምፕ በማስገባት የኢህአዴግን የእርቅ ጥያቄ ተቀበለ። ሰራዊቱን እየነዳ በፈቃደኛት አሳሰራቸው።
በሻዕቢያ አደራዳሪነት ሁርሶ፣ ደዴሳና መስኖ የገባው ሰራዊት “በደባ” ተከቦ ትጥቁን እንዲፈታ ተደረገ። አብጦ የነበረው የኦነግ ጡንቻ በቅጽበት ከሰመ፤ ሰለለ። ኦነግ ሲቆጣጠራቸው የነበሩትን ቦታዎች ለማስተዳደርና በኦህዴድ ለመተካት ኢህአዴግ እንደ እባብ ተሹለክልኮ ዓላማውን አሳካ። ሻዕቢያም በዚሁ ውለታው ኢትዮጵያንና ኢኮኖሚዋን ብሎም የኢትዮጵያን ስነልቦና እንዳሻው እንዲጋልብ ተፈቀደለት። ብዙ አሻጥር ተፈጠረ፤ ተፈጸመም። ደንዳና ቆዳ ያላት ኢትዮጵያና ህዝቧ ተቦጠቦጡ። ተዘረፉ። አንድ እግር የቡና ተክል የሌላት ኤርትራ ቡና ላኪ ከሚባሉት ቀዳሚ አገራት ዝርዝር ውስጥ ተሰለፈች። አፈርን።
“አገሬን ከወራሪ አጸዳሁ” በማለት ከበሮ እየመታ ጦርነት አልቋል ብለው እጅ የሰጡ የወገን ወታደሮችን የረሸነው ሻዕቢያ ኢትዮጵያንም ያስተዳድር ጀመር። ዛሬ የሚማልባቸውና “ውርሳቸውን ሳናዛባ እናስጠብቃለን” የሚባልላቸው አቶ መለስ እንደ ባዕድ መሪ የኢትዮጵያን ክብርና ጥቅም ለሻዕቢያ አሳልፈው ሰጡ። የሻዕቢያ ታጣቂዎችና ኢትዮጵያ አብልታ ያሳደገቻቸው ጎረቤቶቻችን ሳይቀሩ ናጠጡብን። በየደጃቸው መሳሪያ ወደላይ እየተኮሱ በደስታ ውለታ ባስቀመጠችላቸው አገር ላይ ተሳለቁ። ምስኪኖችን ቤት እያስለቀቁ ወረሱ። የሌላቸውን ሃብትና ንብረት ሰበሰቡ። በኤርትራ ምድር በግፍ ለተረሸኑ የኢትዮጵያ ልጆች ተከራካሪ ጠፋና የሞት ሞት ሞቱ። አገራችን የግፈኞች መፈንጫ እንድትሆን መለስ በበረገዱት በር የገባው ሻዕቢያ ከርሱ ሲጎድል፣ “ልክህን እወቅ” የሚሉ ሲነሱ፣ ስርዓት ያዝ ሲባል ደሙ ተንተከተከና የሃይደር ህጻናትን በጠራራ ጸሃይ በላቸው። ትግራይን ወረረ። ሲሰርቁ ኅብረት የነበራቸው ሲከፋፈሉ ተጣሉና አገር ውርደት ገባው።
ይህንኑ ተከትሎ አገር አልበቃ ብሏቸው የነበሩና ወያኔን ሲያገለግሉ የነበሩ ቅጥረኞች የሰበሰቡትን ሳይበሉ ወደ “ከባርነት ናፅነት” ብለው ድምጻቸውን ወደሰጡላት “እናት አገራቸው ኤርትራ” ተጋዙ። ንብረታቸውን በትነው አገር ለቀው ወጡ። ከነጻነት በኋላ “ታይላንድ ትሆናለች፣ ሲንጋፖር ትሆናለች፤ ሆንግኮንግ ትሆናለች” በተባለላት አገራቸው ለመኖር ተገደዱ። ዳቦ ተሰልፈው ለመግዛት ታደሉ። ኬክ በለመደው፣ ቁርጥ በቆርጠው፣ “ሹካ ባስለመደው” እጃቸው ይድሁበት ገቡ። ወታደር ሆኑ። የሰገዱለትና ቅጥረኛ ሆነው ያገለገሉት ህወሃት መልሶ በረሃ በተናቸው። የሚያሳዝነው ግን ኤርትራዊያን ከየመንደሩ ተለቅመው ወደ አገራቸው ሲሄዱ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች አውቶቡስ ከብበው ደረት እየመቱ ያለቅሱላቸው ነበር። ደብቀው ያስቀሩዋቸውም አሉ። ጨርቃቸውን ጥለው አውቶቡስ እንዳይነሳ በፍቅር አምላክ የተንፈራፈሩ ነበሩ። ሁኔታውን የሚያስታውሱ ድርጊቱን “የሞኝ” ተግባር አድርገው ሲወሰዱት ሌሎች ደግሞ “ክፉ ላደረገብህ ክፉ አትመልስ” የሚለው ግብረገብነት የገባቸው የፈጸሙት የጀግንነት ተግባር ነው በማለት የአዲስአበባ ነዋሪዎችን የመንፈስ ልዕልና ያደንቃሉ፡፡
ይህ ከመሆኑ በፊት ጀምሮ ኦነግ ሻዕቢያን ሲለማመነውና እግሩን ሲልሰው የኖረ ድርጅት ዛሬ ድረስ ተበጣጥሶም እዛው አስመራ አምልኮ ደጅ ይገኛል። ከአመት ዓመት ያለ ለውጥ እዛው ይንፏቀቃል። እንደሚሰማው ከሆነ ወታደሮቹ የሻዕቢያ አግልጋዮች ሆነዋል። አመራሮቹም ቢሆኑ አስመራን ለቀው የመውጣትና እንዳሻቸው የመንቀሳቀስ መብት የላቸውም። በዚህም ይሁን በሌላ መነሻ ኤርትራ በከተሙት የተለያዩ የኦነግ ሃይሎች ላይ ከያቅጣጫው ስሞታ መቅረብ ከጀመረ ሰንብቷል። ኤርትራን ለቀው መውጣት አለባቸው የሚለው የኦሮሞ ልጆች ድምጽም በርክቷል። ጥያቄው አያሌ ፖለቲካዊ ማብራሪያ የሚጠይቅና አማራጭ መፍትሄ የሚያሻው ቢሆንም ኤርትራ ውስጥ አሉ በሚባሉ ታጣቂ ተቃዋሚዎች ያልተማረሩና ያልተሰላቹ ቢኖሩ አፍቃሪ ሻዕቢያዎች ወይም ራሳቸው የሻዕቢያ ሰዎች ወይም በማወቅም ሆነ ባለማወቅ የሻዕቢያን ዓላማ የሚያስፈጽሙ ብቻ ናቸው።
እንግዲህ በዚህ መሃል ነው አስመራን ተሳልመው ከነበሩት የኦነግ አመራሮች መካከል አቶ ሌንጮ ለታ፣ አቶ ዲማ ነገዎና ሌሎች ሰሞኑን አዲስ ዜና ይዘው ብቅ ያሉት። አዲስ ፓርቲ በማቋቋም ድፍረት የተሞላው አቋም በማራመድ “አዲሲቷን ኢትዮጵያ በጋራ ለመመስረት ተነስተናል። የቀድሞው የትግል ስልት አያዋጣም” ያሉት። ሃሳቡ መልካም ቢሆንም እንዴት? የሚለው ጥያቄ የበርካቶች ነው። ምክንያቱም በግልጽ “የቀጣዩ ትግል ሜዳ አገር ቤት ነው፤ አገር ቤት ገብተን እንታገላለን” ተብሏልና!
“የኦሮሞ ዴሞክራሲያዊ ግንባር” ODF የሚባል አዲስ ግንባር መቋቋሙ ከአሜሪካ የሚኖሶታ ጠቅላይግዛት ከተሰማበት ጊዜ ጀምሮ በርካታ አስተያየቶችና ጥያቄዎች እየተወረወሩ ሲሆን ከሚመለከታቸው አካላት ጥርት ያለ መልስ አልተሰጠም። ግንባሩ መመስረቱ ይፋ ከሆነ በኋላ መጋቢት 22፤2005ዓም (ማርች 31/2013) በዚያው ጠቅላይግዛት በሚኒያፖሊስ ከተማ በተካሄደ ስብሰባ አንዳንድ ጉዳዮች ይፋ ሆነዋል።
ከብሪታንያ፣ ስዊትዘርላንድ፣ ከካናዳ፣ ከአውስትራሊያ፣ ከጀርመንና ከተለያዩ አገራት የተሰባሰቡ ቁጥራቸው 400 የሚጠጋ ተሰብሳቢዎች ባካሄዱት ውይይት አስፈላጊ የተባሉ ጥያቄዎች ተሰንዝረዋል። ኢትዮጵያን “ኢምፔሪያሊዝም፣ ቅኝ ገዢና ጠላት” አድርገው በመሳል ጥያቄ የሰነዘሩትን ጨምሮ ስለ ቀጣዩ ትግል ትግበራና ሰለ ኦሮሞ ህዝብ ነጻነት መከበር በስፋት ለተነሱ ጥያቄዎች አቶ ሌንጮ ለታ አስገራሚ መልስ ሰንዝረዋል።
“ያለፈውን በመውቀስ የትም አንደርስም። አሁን ማየትና ማሰብ ያለብን ወደፊት ነው። ሌሎች ወገኖችን አግልለን ብንታገል የትም አንደርስም። ያለፈው የትግል መንገድ ስህተት ነበር” ብለዋል። ስለ ኦሮሞ ህዝብ ነጻነት መከበር ሲናገሩ “የሁሉም ኢትዮጵያዊ መብት ካልተከበረ የኦሮሞ መብት ብቻውን ሊከበር አይችልም” በማለት መመለሳቸውን ለማወቅ ተችሏል።
“ጊዜው ተለውጧል። ጊዜው አዲስ ነው። አዲስ ምዕራፍ ላይ ነን። አዲሱ ምዕራፍ ለኦሮሞ ብቻ ሳይሆን ለሁሉም ኢትዮጵያዊ ነው” በማለት የተናገሩት አቶ ሌንጮ፣ “አገር ቤት እንዴት ገብቶ መታገል ይቻላል?” በሚል ለተነሳው ጥያቄ የሰጡት መልስ አዲሱን ድርጅታቸውንና እርሳቸውን የሚፈትን እንደሆነ ያመላከተ ነው።
ቀጣዩ ትግል ኤርትራ ላይ እንደማይሆን በግልጽ የተናገሩት አቶ ሌንጮ፣ አገር ውስጥ በመግባት ለማደራጀት፣ ለመታገል፣ ለመንቀሳቀስ ይቻል ዘንድ “መንገድ እንፈልጋለን” ብለዋል። ኢህአዴግ በተደጋጋሚ እንደሚለው ለድርድር የሚቀመጡ ወገኖች መጀመሪያ ህገመንግስቱን መቀበልና ህግመንግስቱን አክብሮ ለመስራት መማል አለባቸው። ይህ ወደፊት የሚታይ ቢሆንም አገር ቤት ለመግባትና ለመታገል እነ አቶ ሌንጮ ቢስማሙ እንኳን ሌላ መሰረታዊ ችግር እንዳለ ከወዲሁ እየተጠቆመ ነው።
በኦሮሞነታቸው በሚያነሱት ጥያቄ እስር ቤት የታጎሩ የኦሮሞ ልጆች ቁጥራቸው ከፍተኛ ነው – በአስር ሺዎች እንደሚቆጠር ይገመታል። በየቦታው ባሉ እስር ቤቶች ዋናው የመግባቢያ ቋንቋ ኦሮሚኛ እስከመሆን የደረሰበት ሁኔታ ነው የሚታየው። ይህ እውነታ ባለበት አቶ ሌንጮ የሚመሩት አዲሱ ድርጅት እንዴት አድርጎ ይታገላል? ወይም ደግሞ አባላቶቹ እስርና እንግልት እንዳያጋጣማቸው ምን ዓይነት ማረጋገጫና መተማማኛ ማግኘት ይቻላል?
“መልሱ ግልጽ ነው” በሚል ይመስላል “የፈለገው ቢመጣ፣ አስፈላጊው ህግን የጠበቀ ትግል ይካሄዳል። አገሪቱ ላይ ያለውን ህዝብ አስሮ ይችል እንደሆነ የሚታይ ይሆናል” የሚል እንደምታ ያለው ምላሽ ነው እየተሰነዘረ ነው ያለው። በሌላ በኩል አገር ቤት ገብቶ መታገል ብቸኛ አማራጭ ተደርጎ ሲወሰድ አዲሱ ጉዳይ የቀድሞው ሌሎችን ሲያገልና “ልዕልናና ነጻነት ለኦሮሞ ብቻ” በሚል የፖለቲካ ሾፌር ሲደወር የነበረው የትግል ስልት መቀየሩ ነው። በዚህም የተነሳ ይመስላል “ከማናቸውም በኢትዮጵያ ለዴሞክራሲ መረጋገጥና ለህዝብ እኩልነት ከሚሰሩ ድርጅቶችና ፓርቲዎች ጋር አብረን እንሰራለን። የቀድሞው መንገድ አይዋጣም” የሚል ምላሽ የሰጡት።
በኢትዮጵያ ፖለቲካ “እኔን ተከተል፣ ስትቃወም ከኔ ቀመር አትዛነፍ” የሚለውን አመለካከት ጨምሮ በድፍን የአንድ እንቅስቃሴ እርግጠኛ መነሻ ሳይታወቅ አስቀድሞ “የማብከትና የማበስበስ” ስራ መስራት የተለመደ በመሆኑ ከሁሉም ወገን እርጋታ እንደሚጠበቅ፣ ረጋ ብሎ መመርመር እንደሚያስፈልግ ከወዲሁ እየተነገረ ነው።
ላለፉት 20 ዓመታት ኢህአዴግ በብሄር እየለየ በፈጠረው ገደል እየተወረወሩ የሚገቡ ፖለቲከኞች በሰሩት ጥፋት ህዝብ ለከፍተኛ የአእምሮ ጉዳት ተዳርጓል። ኢህአዴግ የ50 ዓመት የቤት ስራ እንደሰጠ አድርጎ የሚያስበውም እነዚሁ የፖለቲካ መሪዎች የህወሃትን የሳሳ ፖለቲካ መረዳት ባለመቻላቸውና ከዋናው ጠላታቸው ይልቅ እርስ በርስ ለመቧቀስ የፈጠኑ መሆናቸውን በቀላሉ ስለሚያሳዩት ነው።
ከ40 ዓመታት የስህተት ጉዞ በኋላ አገር ቤት በመግባት “ሁሉም ነጻ ካልወጡ ኦሮሞ ብቻውን ነጻ አይወጣም” በሚል የትግል መርህ መነሳት በራሱ አስደሳች እንደሆነ አቶ ኦባንግ ሜቶ ለጎልጉል በስልክ ባደረጉት አጭር ቃለምልልስ ተናግረዋል።
“ድንበርና ክልልን ሳይሆን የምንጋራው አብሮነትን ነው” ያሉት የአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄ ዋና ዳይሬክተር “በዲኤንኤ ምርመራ ጎሳ አይታወቅም። ተመሳሳይ ዲኤንኤ ያላቸው ጎሳዎችም የሉም። ሁሉም ነጻ ካልወጡ ማንም ነጻ እንደማይወጣ መስማት ታላቅ ብስራት ነው” በማለት ከዓመታት ትግልና ውትወታ በኋላ ድርጅታቸው ሲታገልለትናሲሟገትለት የቆየው ዓላማ የሌሎችም መርህ ሆኖ በማየታቸውና በመስማታቸው መደሰታቸውን ተናግረዋል።
ከኢትዮጵያ ሕዝብ አብላጫውን ቁጥር የሚይዘው የኦሮሞ ህዝብ ለዚህ ዓይነቱ መርህ ለዘመናት የቆየው ሥርዓቱም ሆነ አኗኗሩ ቅርብ እንደሆነ አቶ ኦባንግ አመልክተዋል፡፡ ድርጅታቸው ከተመሰረተበት ጊዜ ጀምሮ “ከጎሣ ይልቅ ለሰብዓዊነት ቅድሚያ እንስጥ” በሚል የከበረ መመሪያ ላይ ሲሰራ መቆየቱን የገለጹት አቶ ኦባንግ ከዚህ መመሪያ በተጨማሪ “ሁላችንም ነጻ ካልወጣን ማንም ብቻውን ነጻ ሊሆን አይችልም” በሚለው የትግል መርህ በርካታ ስኬቶች መመዝገባቸውን ጠቁመዋል፡፡ ይህንን መፈክር አሁን ደግሞ ኦሮሞ ወገኖቻችን ሲያነሱ መስማት ለድርጅታቸው ታላቅ ድል እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
ስብሰባው ላይ ማንም ሳይጠራቸው በራሳቸው አነሳሽነት እንደሄዱ ያስታወቁት አቶ ኦባንግ “የኦሮሞ ተወላጆች ስብሰባ ሲቀመጡ የሚነጋገሩት ስለ ኢትዮጵያ ነው። ኢትዮጵያዊ ነኝና ውይይቱ ይመለከተኛል። ስለዚህ ተገኘሁ። በደስታ ተቀበሉኝ። በስብሰባው ውስጥ በሰማሁት አዲስ ሃሳብ ተደሰትኩ” ብለዋል።
ላለፉት 20 ዓመታት አንዱ ስለ ሌላው ሲያወራ መኖሩን ያመለከቱት አቶ ኦባንግ ሜቶ አሁን አንድ ላይ በመሆን ለመመካከርና “ለአዲሲቷ ኢትዮጵያ” ግንባታ በጋራ ለመታገል መወሰን ከልምድ የተገኘ የፖለቲካ ተሃድሶ መሆኑን አስታውቀዋል። አያይዘውም ድሮም ቢሆን ፖለቲከኞች እንጂ ህዝብ አእምሮ ውስጥ ያልነበረ አስተሳሰብ በማቀንቀን ለህወሃት ፖለቲካ ማዳበሪያ የማቅረብ ስራ ሲሰራ እንደነበር አመልክተዋል።
አቶ ሌንጮ ለታ እንጀምረዋለን ያሉት አዲሱ መንገድ ሁሉንም ህዝብና የፖለቲካ ድርጅቶች ማዕከል በማድረግ ለመስራት ወስኖ የተነሳ እንደሆነ ሲያስታውቁ ያሰመሩበት ጉዳይ ቢኖር “ያለፈውን አናስብም። አሁን አዲስ ምዕራፍ ላይ ነን። አዲሱ ምዕራፍ ሁሉም የኢትዮጵያ ልጆች ተያይዘው የሚፈጥሯትን አዲስ አገር ማየት ነው፡፡” እርሳቸው እንዳሉት 40 ዓመት ባክኗል። አሁንም መንቃት አግባብ ነው። ነገር ግን ድጋፉም ሆነ ተቃውሞው በተራ የድጋፍና ተቃውሞ ስሜት ሳይሆን ረጋ ብሎ በመመርመር እንደሆነ የሚመክሩ ጥቂቶች አይደሉም።
(ፎቶዎቹን የወሰድነው ከ Hegeree Media channel ቪዲዮ ላይ ነው)

No comments:

Post a Comment