Wednesday, April 10, 2013

“የኢህአዴግ እብሪትና ትዕቢት አገርንና ህዝብን የሚያጠፋ ነው

አቶ ግርማ በቀለ 33ቱ ፓርቲዎች ጊዜያዊ አስተባባሪ ኮሚቴ ዋና ፀሐፊ

ፍኖተ ነጻነት መጋቢት 21 ቀን 2005 ዓ.ም.
የዛሬው እንግዳችን አቶ ግርማ በቀለ ይባላሉ ፡፡ አቶ ግርማ በቀለ በቅርቡ የትብብር ሠነድ የተፈራረሙት 33ቱ ፓርቲዎች ጊዜያዊ አስተባባሪ ኮሚቴ ዋና ፀሐፊ እና የኦሞ ሕዝቦች ዲሞክራሲያዊ ህብረት /ኦህዴህ/የተባለ ፓርቲ ሊቀመንበር ናቸው፡፡
ፍኖተ ነፃነት፡- ፔቲሽን ፈራሚ ፓርቲዎች አሁን በምን እንቅስቃሴ ላይ ናቸው?
Ato Girma Bekele opposition politician based in Ethiopia
አቶ ግርማ በቀለ 33ቱ ፓርቲዎች ጊዜያዊ አስተባባሪ ኮሚቴ ዋና ፀሐፊ
አቶ ግርማ፡- የፔቲሽን ፊርማው ወደ ትብብር ሠነድ ከተሸጋገረ በኃላ በርካታ ተግባራት እየተከናወኑ ይገኛሉ፡፡ የቀጣይ 6 ወራት ተግባር እቅድ ተዘጋጅቷል፡፡ ትብብሩን ለሚቀጥለው 6 ወራት የሚመራ ቋሚ አስተባባሪ ኮሚቴ ለማስመረጥ በዝግጅት ላይ እንገኛለን፡፡ እስከ አሁን ድረስ ስንቀሳቀስ ሁሉም ነገር አልጋ በአልጋ አልነበረም፡፡ ከውስጥም ከውጪም የሚያጋጥሙ ችግሮችን በመቋቋም እዚህ ደርሰናል፡፡ አሁን የደረስንበት ሁኔታ ተስፋ ሰጪ ነው፡፡
ፍኖተ ነፃነት፡- ትብብሩ ስስ ነው፤ ትንሽ ቆይተው አለመግባብት ይፈጥራሉ፤ሁሉም አብረው አይዘልቁም የሚሉ ወገኖች አሉና እርስዎ ምን ይላሉ?
አቶ ግርማ፡- የማራቶን ውድድር አብረው የጀመሩ ሁሉ አይጨርሱም፡፡ እጅግ ውስብስብና ፈታኝ በሆነ ሠላማዊ ትግል አብሮ የጀመረ ሁሉ አብሮ ይጨርሰሳል ተብሎ አይጠበቅም፡፡ ትግሉ እየጠራና እየገፋ በሄደ ቁጥር እየተራገፈና እየተንጠባጠበ ሊቀር ይችላል፡፡ እስከ አሁን በይፋ ለቅቄአለሁ ብሎ በይፋ መግለጫ የሰጠ ፓርቲ ባይኖርም በተግባር ግን እስአሁን አምስት ድርጅቶች ግንኙነታቸውን አቋርጠዋል፡፡ ነገ ሌላ ሊቀጥል ይችላል፡፡ 15 ወይም 20 ፓርቲ ነጥሮ ቢወጣ አያስገርምም ቁምነገሩ ቁጥሩ ላይ አይደለም ዋናው ቁም ነገር ፓርቲዎቹ ሕዝብና አገር የሚፈልገውን ተግባር እያከናወኑ ናቸው ወይ? የሚለው ነው፡፡ ከህዝብ የሚጠበቀው አመራሩን በቅርብ መከታተለና መቆጣጠር ነው፡፡ ድክመቶችንና ችግሮቹን ብቻ እየነቀሱ በማውጣት መተቸት ሳይሆን እኔንም ያገባኛል ብሎ ከትግሉ መቀላቀል ያስፈልጋል፡፡
ፍኖተ ነፃነት፡- ህዝብ ዘንድ እንዴት እንደርሳለን? ህዝቡንስ እንዴት ወደ ትግሉ እናስገባለን ብላችሁ ታስባላችሁ?
አቶ ግርማ፡- ኢህአዴግ ተቃዋሚዎች ከህዝብ እንዳይገናኙ የማያደርገው ጥረት የለም፡፡ ህገመንግስቱን ጥሶ የመሰብሰብ፣ የመደራጀት ፣ሠላማዊ ሠልፍ ማድረግ እየከለከለ ነው፡፡ እኛ ግን መብታችንን ተጠቅመን ትግላችንን እንቀጥላለን፡፡ ዛሬ ሙሉ ለሙሉ በሚባልበት ሁኔታ የሚዲያ አፈና ተደርጓል፡፡ ይሁን እንጂ ያሉትን ሚዲያዎች ሁሉ እንጠቀማለን፡፡ የኤሌክትሮኒክ ሚዲያዎችን ድህረ ገጾችን በመጠቀም ዓላማችንን እናስተዋውቃለን፡፡ የየፓርቲዎችን መዋቅር እንጠቀምበታን፡፡ የሲቪክስ ማህበራትን መዋቅርም እንዲሁም የመንግስት ሚዲያዎችን እንጠቀማለን ፡፡ በተገኘው ቀዳዳ ሁሉ እንጠቀማለን፡፡
ፍኖተ ነፃነት፡- የወቅቱን የአገሪቱን ተጨባጭ የፖለቲካ ሁኔታ እንዴት ይገልጹታል?
አቶ ግርማ፡- እንደ 33ቱ ፓርቲዎች በጋራ ገምግመን የደረስንበት ድምዳሜ የለም፡፡
ጥያቄህን እንደ ግል የማምንበትን ልመልስልህ፡፡ አገራችን ከፍተኛ ችግር ውስጥ የወደቀችበት ጊዜው ነው፡፡ አገራችን ዛሬ በማንኪያ የተያዘች፤ ከሥሯ ድንጋይ የሚጠብቃት እንቁላል ሆናለች፡፡ አገራችን በዚያ ድንጋይ ላይ ወድቃ እንዳትከሰከስ ሁላችንም እጃችንን ዘርግተን እንቁላሏን ለማዳን መጠባበቅ አለብን፡፡ የኢህአዴግ እብሪትና ትዕቢት አገርንና ህዝብን የሚያጠፋ ነው፡፡ የሀገራችን ሁኔታ አሁን ካለበት ወደ ባሰ ደረጃ እየተጓዘ ነው፡፡ ህዝብን እያገለለ ሚዲያን እያፈነ የተለየ ሐሳብ ያለውን ሰው እያጠፋ መጓዝ ይፈልጋል፡፡ ይህ ጉዞ እጅግ አደገኛ ነው፡፡ ህዝቡ ተረድቶታል፡፡ እባካችሁ ተባበሩና ምሩን ሲል ቆይቷል፡፡ እኛም ተባብረናል፡፡ ከእንግዲህ በቁርጠኝነት አገር የማዳን ሥራ መሥራት ይጠበቅብናል፡፡
ፍኖተ ነፃነት፡- አንዳንድ ወገኖች መንግስት በሃይማኖት ውስጥ ጣልቃ እየገባ ነው፣ የተወሰነን ብሔር ለማጥቃት የተነጣጠረ ዘመቻ ጀምሯል ይላሉ፡፡ እርስዎ ምን ይላሉ?
አቶ ግርማ፡- ከጅምሩ የዚህን መንግስት አነሳስ ስንመለከት ገና በረሃ እያለ ዋና ጠላቶች ናቸው ብሎ የፈረጃቸው አሉ፡፡
ከብሔረሰብ አማራን ከሃይማት ኦርቶዶክስን በጠላትነት ፈርጇል፡፡ የብሔር ብሔረሰቦችን ጥያቄ ለመመለስ እነዚህን ሁለቱን ማጥፋት ያስፈልጋል ብሎ አቀደ፡፡ ሁለቱም የአገርና የህዝብ ጠላቶች ናቸው በማለት እንደዓላማ ወይንም እንደ አቅጣጫ አስቀመጠ፡፡ ከተለያየ ቦታ የተገኘ መረጃ የሚያለክተውም ይህንኑ ነው፡፡
ገና ትግራይ ውስጥ በነበሩበት ወቅት ከየቤተክርስቲያኑ ካህናትን በማባረር ቤተክርስቲያኖችን በካድሬ ቄሶች እንዲመሩና እንዲተዳደር አድርጓል፡፡ የመንግስት ሥልጣን ከያዙበት ቀን ጀምሮ በአማራውና በኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ላይ ሲፈፀም የነበረውን ሁሉ የምናውቀው ነው፡፡ ይህን መናገር ለቀባሪው ማርዳት ይሆናል፡፡
ሰሞኑን በአማራው ህዝብ ላይ እየተፈፀመ ያለውንም ይታወቃል፡፡ በቅርቡ ደግሞ የሃይማኖት ት/ቤታችንን ራሳችንን እናስተዳድር የሃይማኖት መሪዎቻችን እኛን አይወክሉም፤ መጅሊሳችንን ራሳችን እንሰይም፤ አህባሽ የተባለ ባዕድ አስተምሮ ከውጭ አምጥታችሁ አትጫኑብን፤ ብለው በሠላማዊ መንገድ የጠየቁ የተከበሩ የሙስሊሙ የሃይማት አባቶች ላይ እየተፈፀመ ያለውን ድርጊት እየተመለከትን ነው፡፡ የሙስሊሙ ህብረተሰብ ለሠላማዊ ትግል አስተማሪ በሆነና በሠለጠነ መንገድ ተቃውሞአቸውን ሲያሰሙ ቆይተዋል፡፡
መማር ለሚችል ከሙስሊሙ ህብረተሰብ ትግስትና ሠላማዊ ተቃውሞን ተምሯል፡፡ የወያኔ/ኢህአዴግ መንግስት ህዝብን በሃይማኖት ከፋፍሎ ለማፋጀትና ዕድሜውን ለማራዘም ያደረገው ጥረት ከሽፎበታል፡፡
የሙስሊሙ ማህበረሰብ አባላት የጠየቁት ጥያቄ መንግስት በሃይማኖታቸው ጣልቃ እንዳይገባባቸው ነው፡፡ ስለዚህ መፍትሔው ከእንግዲህ ሙስሊሙ ክርስቲያኑ መላው የአገሪቱ ህዝብ እጅ ለእጅ ተያይዞ ይህን ሥርዓ ለመቀየር በቁርጠኝነት በጋራ መታገል ነው፡፡

No comments:

Post a Comment