Thursday, January 2, 2014

ዘመቻን በተመለከተ እጭር መልእክት ሞረሽ ወገኔ ለተሰኘው ቡድን ሊቀመንበርና ኣቁዋማቸውን ለሚጋሩ ወገኖች በሙሉ

ከያህያ ጀማል | Jan 1, 2014
barruuእንደሚታወቀው የዳግማዊ ምኒልክን 100ኛ የሙት ኣመት ለመዘከር በበደሌ ቢራ ስፖንሰርነት ቴዲ ኣፍሮ ሊያቀርብ ያቀደውን የሙዚቃ ኮንሰርት በጽኑ በማውገዝ ያገር ቤቱም ሆነ ዳያስፖራው የኦሮሞ ወገን እንዲሁም ቁጥራቸው ቀላል ያልሆነ የኦሮሞ ወዳጆች መጠነ ሰፊ የተቃውሞ ዘመቻ ላይ ይገኛሉ። እስካሁን ይህ ጽሁፍ በሚዘጋጅበት ሰኣት እንኩዋን #BoycottBedele በሚል ርእስ በማህበራዊ ሚድያዎች ላይ የተያዘው ዘመቻ 40,000 ገደማ የሚሆኑ ግለሰቦችን ኣሳትፏል። የተሳትፎው ቁጥር በከፍተኛ ፍጥነት እየጨመረ በመሄድ በኢትዮጵያ የማህበራዊ ሚድያ ኣጠቃቀም ታሪክ ውስጥ የመጀመሪያውን ደረጃ ይዟል። ይሄም ዝም ብሎ ጩሄት ሳይሆን ጉዳዩ የሚመለከታቸውን ወገኖች ትኩረት ስቦ የተሳሳተውን ኣቅዋማቸውን መልሰው እንዲያስተካክሉ ተጽእኖ ሲያሳርፍባቸው እየታየ ነው።
የሞረሽ ሊቀመንበርና የሊቀመንበሩን ኣቁዋም የምትጋሩ ወገኖች ሆይ! የኦሮሞ ህዝብ ምኒልክን የሚያወግዝበት ምክንያት ከናንተ የተሰወረ ኣይደለምና ያንን በማብራራት የኣንባቢዎችን ጊዜ ማባከን ኣልፈልግም። ምኒልክ ለናንተ ጀግናችሁ ሊሆን ይችላል። ለኛ ለኦሮሞና ለኣብዛኛው የኢትዮጵያ ብሄር ብሄረሰቦች ግን ምኒልክ ኣፍሪቃዊ ሂትለር ነው ቢባል ማጋነን ኣይሆንም። ስለሆነም እኛ ኦሮሞዎችና እንደኛ ሁሉ የምኒልክ ጭፍጨፋ ሰለባ የሆኑ የደቡብ ብሄር ብሄረሰብና ህዝቦች ኣፄውን በጨካኝነቱ ስናስብ እናንተ ግን በጀግንነቱ እየዘከራችሁ ነው። ኣንዱና ትልቁ መለያያ ነጥባችንም ይሄው ለየቅል የሆነው የታሪክ መስተዋታችን ነው።
ስለ ኣመለካከታችን ልዩነት ይህን ያህል ካልኩ ዘንዳ ይቺን መልእክት ለመጫጫር ወዳነሳሳኝ ፍሬ ጉዳይ ልዝለቅ። በህብር ሬድዮ ጋባዥነት የሞረሹ ሊቀመንበር የተናገሩትን ፍሬ ጉዳይ በጥንቃቄ ኣድምጫለሁ። ሊቀመንበሩ ሲናገሩ የኦሮሞ ህዝብ በተለይም ወጣቱ ትውልድ የያዘውን ብሄርተኛ ኣቁዋም ለማጥላላት የተቻላቸውን ያህል ሞክረዋል።  የኦሮሞ ምሁራን የሚደልቁት ከበሮ በሻዕቢያና ወያኔ የተቀነባበረ አማራና ኦሮሞን ለማጋጨት የተወጠነ ልቦለድ ነው።’ ሲሉ ያለሃፍረት ተናግረዋል። ሊቀመንበሩ ይህንን ሲናገሩ ኦሮሞና ኣማራ እንዳይጋጭ በጣም የተጨነቁ መስለው ለመቅረብ ቢደክሙም ኣልተሳካላቸውም። ሁለቱ ብሂሮች እንዳይጋጩ የሚመኝ ቅን ልቦና ቢኖራቸው ኖሮ የኦሮሞ ምሁራን ያነሱትን የጸረ ምኒልክ ተቃውሞ ‘ከበሮ መደለቅ፣ ልቦለድ…’ እያሉ ከማጥላላት ይቆጠቡ ነበር።
የዚህ መልእክት ትልቁ ኣላማ ግን የግጭት ጉዳይ ኣይደለም። ሊቀመንበሩ የተናገሩት ‘የኦሮሞ ምሁራን የሚደልቁት ከበሮ በሻእብያና ወያኔ የተቀነባበረ…’ የሚለው ነጥብ ላይ ያተኮረ መሆኑን ላሰምርበት እወዳለሁ። የግለሰቡ መልእክት እምብዛም ውሃ መቁዋጠር የማይችል ቢሆንም ኣባባላቸው ከዚህ ቀደምም በተለያዩ ኣጋጣሚዎች ኣንዳንድ የኣማራ ልህቃን ሲያስተጋቡት ከኖሩት መሰል ኣስተያየት ጋር ስለሚገጣጠም ተንቆ መታለፍ የሌለበት ሆኖ ኣገኘሁት። የኦሮሞን ህዝብ የጭቆና በቃኝ ድምጽ ለማጥላላት ሲባል ከድምጹ በስተጀርባ ያለው እገሌ ነው የሚል በንቀት የተጠናወተ ኣቁዋም ሲራመድ የሞረሹ ሊቀመንበር የመጀመሪያው ኣይደሉም ማለቴ ነው። ኦሮሞ እንደብዙሃንነቱ ተደራጅቶ ሃይል መሆን የመቻሉን ሎጂካዊ እውነታ ኣምነው መቀበል የማይሆንላቸው ወገኖች መኖራቸውን እናውቃለን። እንደነዚህ ወገኖች እምነት ከሆነ የኦሮሞ ተወላጆች ይህን ያህል በሚያስድነግጥ ቁጥር ተደራጅተው ማህበራዊ ሚድያን በመጠቀም የሚቃወሙትን በመቃወም ወይም የሚደግፉትን በመደገፍ ጎላ ያለ ድምፃቸውን ለፈለጉት ኣካል ማሰማት ኣይችሉም። ኦሮሞዎች ይህን ለማድረግ የግድ የሆነ ሌላ ኦሮሞ ያልሆነ ሃይል ከበስተጀርባቸው መኖር ኣለበት። በተለይም እንዲህ ያለውን የኣማራውን ፅንፈኛ ወገን የማያስደስቱ መሰል እንቅስቃሴዎች የወያኔ እገዛ ሳይታከልባቸው በኦሮሞ ብቻ ተከናውነው ሊሰምሩ ኣይችሉም የሚለው ኣስተሳሰብ ወይም ማስመሰያ የሚያስተላልፈው መልእክት ቢኖር ኣንድና ኣንድ ብቻ ነው። የኦሮሞን ህዝብ መናቅ። ኦሮሞ በጭራሽ ብቻውን ቆሞ እንዲህ ያለ ታሪክ መስራት የማይችል ኣስመስሎ ለማሳመን የሚደረግ ጥረት ነው። እንዲህ ያለው ኣቀራረብ ኣንዳንዴ ከኣስገራሚነቱ ኣልፎ ኣስቂኝ ነው። ቁጥራቸው ቀላል ያልሆነ የኣማራው ጽንፈኛ ወገኖች ይባስ ብለው ጭራሽ የኦሮሞ ህዝብ የባህል፣ የቁዋንቁዋና ራሱን በራሱ የማስተዳደር ጥያቄ ከወያኔ የተኮረጀ ኣስመስለው እስከማቅረብ የሄዱበት ኣጋጣሚ ብዙ ነው። እንደዚህ ያሉ ሰዎች ማንን ለማታለል እንደከጀሉ ግልጽ ኣይደለም።
የሞረሹን መሪም ሆነ መሰል ኣቁዋም የሚያራምዱ ወገኖች ከኦሮሞ ህዝብ ጋር እንደ ኣዲስ መተዋወቅ ያስፈልጋቸዋል። ወያኔን በወያኔነቱ፣ ራሱን ችሎ በሌላ ኣገር መሪነት የሚታወቀውን ሻእቢያም በጎሮበት ማንነቱ ለይተው በማወቅ ሃራምባና ቆቦን ከመደበላለቅ ተቆጥበው በተለይም በኦሮሞ ህዝብ ጉዳይ ላይ የሚጠቀሟቸውን ቃላት በጥንቃቄ መምረጥ ይጠቅማቸዋል። የኦሮሞን ህዝብ ለመናቅ ሲባል የህዝቡን ጥያቄ ከወያኔ ወይም ከሌላ ሃይል ጋር ለጥፎ መዘባረቅ ኣጉል ከመጃጃል ያለፈ ምንም የፖለቲካ ፋይዳ ኣያስገኝም።
የሞረሹ ሰውና መሰሎቻችሁ ሆይ!
ከመቶ ኣመታት በፊት በህይወት የነበረው የናንተ ጀግና ምኒልክ ኣንድ ብሎ ያስተማራችሁ ነገር ቢኖር ኦሮሞን በኦሮሞነቱ መናቅ ነው። ምኒልክ በዘመኑ ኦሮሞን ሊንቅ የቻለው ከኣውሮፓ በተገኙ ዘመናዊ የጦር መሳሪያዎች ተመክቶ ሰራዊቱንም እነዚህን ዘመናዊ መሳሪያዎች እሳክፍንጫው በማስታጠቅ ጦርና ጎራዴ ብቻ የያዘውን የኦሮሞውና ሌላውም መከታ ኣልባ ወገኔን በጭካኔ ጨፍጭፎ ማስገበር በመቻሉ ነው። ዛሬ ላይ ያለው የኣማራ ትውልድ ጽንፈኛ ወገን ግን እንዲህ ያለውን ከኣባቶቹ የወረሰውን ትምክህታዊ ንቀት እንዳለ ለማስቀጠል ሲንደፋደፍ ይገርመኛል። ኦሮሞን መናቅ ትላንት ባህላቸው ያደረጉ ወገኖች የወግ ነገር ሆኖባቸው ዛሬም የንቀት ባህላቸውን እንዳለ ማስቀጠሉ ኣጸፋው ኣደገኛ ይሆናል። ሁላችንም 21ኛውን ክፍለ ዘመን ኣብሬን እየኖርነው መሆኑ የተረሳ ይመስላል። ናቂው ወገን 21ኛ ክፍለ ዘመን ላይ ሆኖ ተናቂው ደግሞ 19ኛው ክፍለ ዘመን ላይ ተገድቦ የሁዋሊዮሽ የቀረ እስኪመስል ድረስ ከኣማራው ጽንፈኛ ወገን ዘንድ የምናስተውለው ኦሮሞ ላይ ያነጣጠረ ስልተ-ብዙ ንቀት የጤና ኣይደለም።
የሞረሹ ሰውም ሆኑ መሰሎቻቸው ማወቅ ያለባቸው ኣንድ ሃቅ ኣለ። የኦሮሞ ህዝብ የማንም ድጋፍ ሳያስፈልገው ራሱን ችሎ ይበጀኛል ያለውን የትግል ጎዳና ቀይሶ በመገስገስ ላይ የሚገኝ ንቁ የ21ኛው ክፍለ ዘመን ህዝብ ነው። የብሄር መብቱን ለማስከበር የሚያነሳው ጥያቄ የ50 ኣመት እድሜ ያለው ጥያቄ መሆኑ ከህሊናችሁ የተሰወረ ባይሆንም ገና ትላንት ስልጣን ከጨበጠው ወያኔ ጋር ኣስተሳስራችሁ ለማቅረብ መድከማችሁ ምናልባት ከፍራቻ የመነጨ ሊሆን ይችላል። ፍራቻን ደግሞ በዚህ መልኩ መዳፈር ተጨማሪ ኣስፈሪ መዘዞችን ከማስከተል የዘለለ ጥቅም ኣያስገኝላችሁም። ወያኔ እንደሆን ላለፉት 23 ኣመታት በጋራ ስናወግዘው የኖርን ኣምባገነን ሃይል መሆኑን እስከመዘንጋት ሄዳችሁኣል። ኣንድ ስልጣን ላይ ያለ ኣምባገነን ሃይል መብቴ ታፈኔ ብሎ ከሚታገል ተቃዋሚ ወገን ጋር ኣንድ ላይ የሚደመርበት ምንም ኣይነት ሎጂክ ኣይኖርም።
ይሁን እንጂ ከወያኔ ጋር የሚያመሳስለን ጉዳይ ሲኖር በስመ ጠላትነት ብቻ ኣይናችንን ጨፍነን ወደ ተቃራኒው ኣቅጣጫ በመነዳት ጥቅማችንን ኣሳልፈን የምንሰጥ ጅሎች ኣይደለንም። ከኣማራው ለዘብተኛ የፖለቲካ ሃይል ጋርም እንዲሁ። ማንኛውም ወገን የጋራ ጥቅማችንን በሚያስጠብቅ ጎዳና ላይ ከተቀላቀለን ታሪክን ለታሪክ ትተን ለመጻኢ እድላችን ኣብሬን የማንገሰግስበት ምክንያት ኣይኖርም። እንደ ትላንቱ ሁሉ ዛሬም የራሱን ፍላጎት በሃይልና በብልጣብልጥነት እኛ ላይ ለመጫን ያደባ ሃይል ካለ ግን እሱ የነጋበት ጅብ መሆኑን ላስታውሰው እወዳለሁ። ኣረቦች ሲተርቱ ‘ውሾቹ ይጮሃሉ ግመሎቹም ይገሰግሳሉ’ እንደሚሉት ሁሉ ትግላችንም በኣጉል ጩሄቶች ተደናብሮ ከግስጋሴው የሚገታ ኣይደለም
ቸር እንሰንብት!
ያህያ ጀማል
ለኣስተያየትዎ   gulummaa75@gmail.com

No comments:

Post a Comment