Tuesday, June 3, 2014

“የ መለስ ዜናዊ ሚስጥሮች …..በተስፋዬ ገ/አብ” – Tesfaye G.Ab

በየእለቱ አዳዲስ ዜናዎች እንሰማለን። ለአብነት “ስዩም መስፍን በቻይና የኢትዮጵያ አምባሳደር ሆነ” የሚለው ተራ ዜና ነበር። “ስዩም ተወረወረ” ብለን ያመንንም ነበርን። ስዩም ሌላ ተልእኮ እንደተሰጠው ለመረዳት፣ የቻይናና የወያኔን የንግድ ስምምነቶች ማስላትና አንዳንድ አንጓዎች ብቅ እስኪሉ መጠበቅ ያስፈልግ ነበር። አባይ ፀሃዬ የስኳርና የጨው ሚኒስትር ሆኖ ሲሾም ብዙ ስላቆች አንብቤ ነበር። የአባይ ፀሃዬን አንገት የስኳር ጆንያ ውስጥ በመክተት ያላገጡ ሜዲያዎችም ነበሩ። ሆኖም የስዩምም ሆነ የአባይ ምደባዎች ቀጣዩን የወያኔ ዋና ዋና እቅዶች ጠቋሚ ነበሩ። የስዩምን ሹመት ተከትሎ፣ የወያኔ ባለስልጣናት ልጆች ለትምህርት ወደ ቻይና ተላኩ። እነዚህን ልጆች በኮሚኒስታዊ አስተሳሰብ አደራጅቶ ማዘጋጀት የሽማግሌው የትርፍ ጊዜ ተልእኮ መሆኑ እየተሰማ ነው።
ወያኔ የጦር መሳሪያ በብዛት እየገዛና እያመረተ ነው።

ጦር መሳሪያ የማከማቸቱ እውነተኛ አላማ ምን ይሆን? በአባይ ጉዳይ የግብፅን ጦር ለመመከት? ይሄ የተበላ እቁብ ሆኖአል። ትግራይን ለመገንጠል ቆርጠው ወስነው፣ በሹክሹክታ እንደሚሰማው TDF (Tigray Defense Force) የተባለውን ይፋ ያልሆነ መስሪያ ቤት በምስጢር እያደራጁ ይሆን?
የህወሃት ሰዎች ትግራይ በጠላት ተከባለች ብለው ማመናቸው ወይም እንዲታመን መፈለጋቸው የችግሩ ማእከል ይመስላል። “እንደ እስራኤል በጉልበታችን መኖር እንችላለን” የሚለው ቅዠት ውስጥ የገቡት አምነውበት ነው ወይስ ለፕሮፓጋንዳ ፍጆታ? ይህን በትክክል ማወቅ አይቻልም። ህዋሃት የትግራይን ህዝብ እንደመሸሸጊያ ሊያመቻቸው ካላሰበ በቀር፣ የትግራይ ህዝብ የጎረቤት ጠላት የለውም። ሊኖረውም አይችልም። በፍቅር የመኖር ሰፊ እድል እያለ ግጭት ብቻ ለምን አማራጭ ሆኖ ይቀርባል?
“ወያኔ ስልጣን ላይ ለመቆየት የቀረችው አንድ የማጭበርበሪያ ካርድ አሰብን በጦር ሃይል መያዝ ናት። የጦር መሳሪያ ማከማቸቱም ለዚያ ኦፕሬሽን ሊሆን ይችላል” እያሉ የሚተነትኑ፣ በተዘዋዋሪም የሚገፋፉ አሉ።
በርግጥ ኢትዮጵያና ኤርትራ ወደ ጦርነት ከገቡ ውጊያው አሰብ ላይ ብቻ ሊሆን እንደማይችል ግልፅ ነው። እና ይሄ ትንተና ውሃ አይቋጥርም። ካልሆነ ታዲያ የወያኔ የተጋነነ የጦር መሳሪያ ክምችት አላማ ምን ሊሆን ይችላል? በርግጥ ከዚሁ ጋር ተያይዞ የኢትዮ-ኤርትራ የድንበር ጉዳይ በእንጥልጥል የተያዘበት ያልተገለፀ ምክንያት እንደሚኖረውም አስባለሁ።
ያልተመለሱልኝ እና የመጨረሻ አንጓቸውን ያላወቅሁዋቸው ጥያቄዎች ከጥቂት በላይ ናቸው። የመሬት ሽያጩ የመጨረሻ አንጓ ገና ግልፅ አልሆነም። ልማት አለመሆኑ ግልፅ ነው። የኮሚሽን ገንዘብ ለማግኘትና ለመዝረፍ ብቻ ተብሎ ሊታለፍም አይችልም። በርግጥ በዚህ ጉዳይ ላይ የራሴ ጥርጣሬ አለኝ። ጊዜውን አላስታውስም። ሆኖም እኔም በተሳተፍኩበት አንድ የፕሮፓጋንዳ ካድሬዎች ስብሰባ ላይ፣ መሬትን የመሸጥና የመለወጥ አጀንዳ ተነስቶ ነበር። ቃል በቃል የመዘገብኩት ባይሆንም፣ በረከት ስምኦን የተናገረው አይረሳኝም፣
“በዚህ ዘመን መሬት ይሸጥ ይለወጥ ብንል ያልተነካ ሰፊ ድንግል መሬት ያለው በደቡብና በኦሮሚያ ነው። የመሬት ሽያጭ ከፈቀድን መሬት ሊገዛ የሚችለው ገንዘብ ያለው ባለሃብት ነው። በዚህ ዘመን ገንዘብ ያለው ማን እንደሆነ ደግሞ ይታወቃል። በዚህ ወቅት መሬት እንዲሸጥ ከፈቀድን ቀደም ሲል ነፍጠኛው በጠመንጃ ይዞት የነበረውን መሬት አሁን ደግሞ መልሶ በገንዘቡ እንዲቆጣጠረው መፍቀድ ማለት ነው…”
3
ኢህአዴግ ስልጣኑን ከለቀቀ የመሬት ፖሊሲው እንደሚቀየር ያውቀዋል። ስለዚህ ዋጋ ያለውን መሬት ሁሉ ከወዲሁ ሸጦ መጨረስ ይፈልጋል። ዛሬ መሬቱ ለውጭ ዜጎች ተሸጦ ካለቀ ወደፊት መሬት የመግዛት አቅም ያለው ኢትዮጵያዊ ቁራሽ መሬት ሊያገኝ አይችልም። ቢያገኝ እንኳ ውድ ይሆንበታል። ለ50 አመት ውል የተፈረመለትን ህንዳዊ ማባረርም ቀላል አይሆንም። ምክንያቱም ብዙ ችግር ያስከትላል። ሙሴቪኒ ስልጣን ይዞ ምእራባውያንን እርዳታ ሲጠይቅ፣ በቅድሚያ ኤዲአሚን ዳዳ ያባረራቸውን ህንዶች መሬትና ንብረት እንዲመልስ ነበር ያዘዙት። ሳይወድ አፍንጫውን ተይዞ መለሰ። የአማራ ባለሃብቶችን ማዳከም፣ የኦሮሞ ባለሃብት እንዳይፈጠር ማገድ የወያኔ ግንባር ቀደም መርህ መሆኑ ግልፅ ነው። መሬት በችኮላ እንዲህ የሚቸበችቡበት ምክንያት ከዚሁ ጋር የተያያዘ ይመስላል።
በርግጥ “ኢትዮጵያዊው ባለሃብት ቡና ቤት ከመገንባት አያልፍም” እያሉ የሚያላግጡ አሉ።
መቼ ተሞከረና?
እንኳን በዚህ ዘመን፣ በ60ዎቹ መጀመሪያ ላይ ወጣቶች ቦሎቄ እያመረቱ ወደ ውጭ መላክ ጀምረው ነበር። ወያኔ የሃገሪቱን መሬት ለውጭ ሰዎች ሸጦ የማጠናቀቅ ተልእኮ እንደያዘ ብዙ አስረጅ ማቅረብ ይቻላል።
ለአብነት ከአዲሳባ ናዝሬት በግማሽ ሰአት ውስጥ መግባት የሚያስችል ዘመናዊ መንገድ ተሰርቶ በመጠናቀቅ ላይ ነው። የዚህ መንገድ መገንባት አላማ፣ “ወደ ናዝሬት በፍጥነት ለመድረስ ነው” ብሎ የሚያስብ የዋህ የሚኖር አይመስለኝም። ወያኔ ከአዲሳባ ናዝሬት በፍጥነት ስለመግባት ሊያሳስበው አይችልም። የመንገዱ መገንባት ሁለተኛ አንጓ፣ ከአዲሳባ ናዝሬት በሚዘረጋው አዲስ መንገድ ግራና ቀኝ ያለውን መሬት ለቻይናና ለቱርክ ለመሸጥ ያለመ ነው። ምክንያቱም በደብረዘይት በኩል ያለውን መሬት ሸጠው ጨርሰውታል። ይህን ማድረግ ለሃገርና ለህዝብ እንደሚጠቅም የሚያሳምን ማብራሪያ እስካሁን አላነበብኩም። መለስ እራሱ ለውጭ ባለሃብቶች መሬት መሸጥ ጉዳት መሆኑን ሲናገር ተደምጦአል። ዚምቧቡዌ በተመሳሳይ መሬቷ እንዲህ ተበዝብዞ ነበር። ሙጋቤ መሬት ለማስመለስ በተነሳበት ወቅት ሃገሪቱ የገጠማት መከራ ግን መቼ እንደሚያቆም እንኳ አልታወቀም። ኢትዮጵያዊው ዜጋ የገዛ መሬቱን መጠቀም እንዳይችል በአዋጅና በፖሊሲ አግደህ፣ ለውጭ ባለሃብት በርካሽ ዋጋ መቸብቸብ ልማታዊ አላማ ይኖረዋል?
“አንጓ” ያልኩትን በቀላሉ ለማስረዳት ብዙ ሰው የሚያውቀውን አንድ ምሳሌ ልጥቀስ።
“….በምርጫ 97 ህዝቡ እንደሚያምፅ ታወቀ – አመፀኛውን ለማስቆም የሚቻለው ከሰልፈኞቹ ጥቂት በመግደል መሆኑ ታመነበት – ግድያውን መሸሸግ ስለማይቻል ለአለማቀፍ ትችት መጋለጥ እንደሚኖር ግልፅ ሆነ – ስለዚህ ለሚገደሉ ሰዎች ግድያ በቂ ምክንያት ማቅረብ እንደሚገባ ታመነ – “ሰልፈኛውን የገደልነው፣ ስንከላከል ነው” ብለው ቢከራከሩ እንደሚታመኑ ገመቱ – ለዚህ ደግሞ ጥቂት ፖሊሶች መሞት አለባቸው ተባለ – ስለዚህ ፖሊሶችን የሚገድል ሌላ ሃይል ተዘጋጀና እንደታቀደው ተፈፀመ…”
“የመጨረሻው አንጓ” የፖሊሶቹ መገደል ለፍርድ ቤት ክርክር እንዲመች ተብሎ የተፈፀመ መሆኑ ነበር። ወደፊት ሊሆን የሚችለውን ቁጭ ብለው ወረቀት ላይ እንደ ሂሳብ ይሰሩና በቅደም ተከተል፣ አንጓዎችን በእቅድ ያስኬዷቸዋል። ይህ የተለመደ የወያኔ አሰራር ሲሆን በሙያውም ተራቀውበታል።
4
“አማርኛ ቋንቋን ከስራ ቋንቋነት ማቋረጥ” ከወያኔ ፕሮጀክቶች ሁሉ አስቸጋሪው ነበር። ምክንያቱም በረጅም ጊዜ የተገነባን ባህልና ቋንቋ፣ እንደ ግድብ በአንድ ፈንጂ መደርመስ አይቻልም። ከዚያም ባሻገር ስራው፣ “የራስ ቋንቋን መጠቀም” በሚል ሽፋን የሚሰራ በመሆኑ ፈታኝ ለመሆን በቅቶአል። አዲስ አበባ በሚገኙ አንዳንድ የግል ትምህርት ቤቶች፣ “አማርኛ መናገርና ድንጋይ መወርወር ክልክል ነው” የሚል ማስታወቂያ ሲለጠፍ መንግስት አይቶ እንዳላየ ዝምታን መርጧል። የአፋር ክልል ከአማርኛ ጋር ተጣብቆ አስቸግሮ ነበር። በዚህ አመት ግን አማርኛን ከአፋር ማስወገድ ተቻለ። የዜና ዘገባውን ስሜታዊነት ላስተዋለ የአፋር ክልል ከአማርኛ ሳይሆን፣ ከፖሊዮ ነፃ የሆነ ነበር የሚመስለው። ከጥቂት ጊዜ በሁዋላ አፋር ላይ አማርኛ ከመናገር ዋሽንግተን ዲሲ ላይ አማርኛ መናገር ሊቀል ይችላል። ለደቡብ ህዝብ አባይ ፀሃዬ “ወጋጎዳ” የተባለ ቅይጥ ቋንቋ ፈልስፎላቸው ነበር። የወጋጎዳ ቋንቋ መማሪያ በ7 ሚሊዮን ብር ሜጋ ማተሚያ ቤት ታትሞ ነበር። መፅሃፉ መሰራጨት ሲጀምር ህዝቡ አመፀና ከሸፈ። መፃህፍቱም ከጥቅም ውጭ ሆኑ። የማሳተሚያ ገንዘቡን ግን ደቡብ ክልል ለሜጋ ከፈለ። ከዚያ ወዲህ ግን ደቡቡን ከአማርኛ ለማላቀቅ ሌላ ዘዴ ማግኘት ሳይችሉ ቀርተዋል። ለነገሩ የአማራ ክልል መሪ በረከት ስምኦን፣ አማርኛን እየተጠየፈ ለአማርኛ ቋንቋ እድገት ይሰራል ተብሎ ሊጠበቅ አይችልም።

No comments:

Post a Comment