Tuesday, May 14, 2013

2 የወያኔ ኢህአዲግ ሥርዓት የሃገር ውስጥ አልበቃ ብሎት በስደት ሃገር የተቋቋሙትን የኢትዮጵያ ኦርተዶክስ አብያተ ክርስቲያናትን በጎሳ አፓርታይድ ሥርዓት ሥር ለማዋል የሚያደርገው ጥረት።

የወያኔ ኢህአዲግ ሥርዓት የሃገር ውስጥ አልበቃ ብሎት በስደት ሃገር የተቋቋሙትን የኢትዮጵያ ኦርተዶክስ አብያተ ክርስቲያናትን በጎሳ አፓርታይድ ሥርዓት ሥር ለማዋል የሚያደርገው ጥረት።

በአውሮፓ ውስጥ አንጋፋ የምትባለውና ከፍተኛ እድገት በማሳየት የምትታወቀው ርዕሰ አድባራት ለንደን ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ከቅርብ ጊዜ ጀምሮ በከፍተኛ ሁከትና ረብሻ ውስጥ እንደምትገኝ በተለያዩ ድህረገጾች ላይ ከሚወጡ መረጃዎች ለመረዳት ችለናል።
London Ethiopian Orthodox Church
ለንደን ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያንን
ጉዳዩን ቀረብ ብለን እንደተረዳነው በቤተ ክርስቲያኗ ውስጥ የተፈጠረው ችግር ቢቻል በሰላምና እርቅ፤ ካልሆነም ደግሞ የቤተ ክርስቲያኗ ሕጋዊ ባለቤት የሆኑት አባላቷ በነፃነት ተወያይተው በሚያስተላልፉት ውሳኔ እልባት ሊያገኝ በቻለ ነበር። ይህ ሁሉ ተሞክሮ ካልተሳካ ደግሞ የቤተ ክርስቲያንን ሕግና ቤተ ክርስቲያኗ የምትገኝበትን ሃገር ሕግ ተከትሎ ችግሩ እልባት ማግኘት ሲገባው የዚህ ሁሉ ችግር ምንጭ የሆኑትና ስልጣንን የሙጥኝ ብለው አለቅም ያሉት የቤተ ክርስቲያኑ አስተዳዳሪ ቆሞስ አባ ግርማ ከበደና ደጋፊዎቻቸው የሆኑ ጥቂት ካህናትና የሰንበት ት/ቤት ወጣቶች አብላጫውን የቤተ ክርስቲያኗን አባላት በማግለል ሌሎች ከቤተ ክርስቲያኗ ጋር በአቋም የተለዩ ሆነው በለንደን የሚገኙና በወያኔ አህአዲግ ቀጥተኛ አመራር ሥር ከሚገኙ ከገብረኤልና ከስላሴ አብያተ ክርስቲያናት የተወሰኑ አባላት ጋር በማበር በተለይም አባ ጳውሎስ በትግራይ ተወላጅነት መርጠው የሾማቸው አቡነ እንጦስና ሌላው የትግራይ ተወላጅ የሆኑት መጋቢ ተወልደ ወልደማርያም ጋር እየተመሳጠሩ ብዙ ተንኮልና ሴራ ሲሸርቡ ከቆዩ በኋላ ኢትዮጵያ ካለው ከቤተ መንበረ ፓትርያርክ ጋር በመነጋገር አባላትን ሳያማክሩና ሳያስፈቅዱ ከኢትዮጵያ ጳጳስ በማስመጣት ቤተ ክርስቲያኗ በወያኔ ኢህአዲግ ሹመኞች ቁጥጥር ሥር እንድትውል በመጣር ላይ ይገኛሉ።
በዚህ የተንኮል ሴራ መሠረትም በአሁኑ ወቅት በወያኔ ኢህአዲግ የተወከሉ አቡነ ገብረኤልና አቡነ ቀውስጦስ የሚባሉ ጳጳሳት ከአዲስ አበባ ወደ ለንደን መላካቸው የታወቀ ሲሆን ዓላማቸውም ቤተ ክርስቲያኗ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን አካል ነች የሚል ሕጋዊ የሚሉትን ጥያቄ በማንሳት የቤተ ክርስቲያኗ አስተዳደርም ሆነ ንብረቷ በቀጥታ በወያኔ ኢህአዲግ ሥርዓት ምርጫና ሹመት ለንደን ላይ በተቋቋመውና በአቡነ እንጦስና በመጋቢ ተወልደ ወልደማርያም የበላይ ኃላፊነት በሚመራው የሰሜን አውሮፓ ሃገረ ስብከት ሥር እንዲውል ለማድረግ ነው።
ይህ የሰሜን ምእራብ አውሮፓ ሃገረ ስብከት (ETHIOPIAN ORTHODOX TEWAHEDO CHURCH DIOCESE OF NORTH WEST EUROPE) በሚል በወያኔ ኢህአዲግ ሹመኞች አማካኝነት ከ2011 ጀምሮ በUK Charity commission ተመዝግቦ የተመሠረተው ተቋም ሲሆን ወያኔ ኢህአዲግ በአውሮፓ ውስጥ ያለው ስደተኛ ኢትዮጵያዊ በጥረቱና በድካሙ ያቋቋማቸውን የኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያናት በቀጥታ ትዕዛዝ ሥር ለማዋልና ሃብትና ንብረታቸውን ለመቆጣጠር እንዲያስችለው ታስቦ የተቋቋመና የተደራጀ  የሥርዓቱ ቅርንጫፍ ነው።
(እዚህ በመጫን የመረጃውን ትክክለኛነት ያረጋግጡ)
ሃገር ስብከት በማለት ወያኔ ኢህአዲግ ለንደን ላይ ያቋቋመውን የቻሪቲ ድርጅት በበላይነት የሚመሩት ኃላፊዎች (Trustees) በቁጥር 9 ሲሆኑ ከነዚህ ውስጥ 6ቱ በትክክል የተረጋገጠ የትግራይ ጎሳ አባላት ናቸው።
ከዚህ በተጨማሪ እንደ ኢትዮጵያ አቆጣጠር በ1997 ዓ/ም ኢትዮጵያ ውስጥ ከ200 በላይ ህፃን፤ ወጣት፤ አሮጊትና ሽማግሌ በወያኔ አግአዚ ወታደር በግፍ ሲገደሉና ከ30.000 በላይ ወጣቶች በየ እስር ቤቱ ታጉረው፤ ሲገረፉና ሲሰቃዩ፤ ከዚህም በተጨማሪ ሃምሳና 60 ሰው በአንድ ምላጭ ስላጩ፤ የርዕሰ አድባራት ለንደን ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን አባላት በወገናቸው የሚደረሰውን ግፍና በደል በማየት ኢትዮጵያ ውስጥ በወያኔ ሥርዓት አማካኝነት በግፍ ለተገደሉት ወገኖቻችን በቤተ ክርስቲያናችን ውስጥ ጸሎት ይደረግ፤ ከዚህም በተጨማሪ ሥርዓቱ በሰብዓዊ ፍጡር ላይ የፈጸመውንና በመፈጸም ላይ የሚገኘውን በደልና ግፍ እንዲያቆም ቤተ ክርስቲያናችን እንደ ቤተ ክርስቲያን የተቃውሞ ድምጿን በማሰማት ከተበደለውና ግፍ ከሚፈጸምበት ሕዝባችን ጎን ትቁም በማለት ሲወስኑ እነዚህ ዛሬ ወያኔ አህአዲግ ሃገረ ስብከት ብሎ ባቋቋመው ቻሪቲ ውስጥ መሪ እንዲሆኑ የተደረጉት አባዛኛዎቹ ሰዎች በወቅቱ በርዕሰ አድባራት ለንደን ደብረጽዮን ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ይገኙ የነበረ ሲሆን የሕዝብን ውሳኔ ባለመቀበል ከወያኔ ኢህአዲግ ጋር በመወገን ኢትዮጵያ ውስጥ በግፍ ለተገደሉ ሰዎች ጸሎት አይደረግም ብለው ተቃውሞ በማቅረብ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ በግፍ ለተገደሉ ወገኖች ጸሎት ሲደረግ ቤተ ክርሲቲያንን ረግጠው የወጡ ሰዎች ናቸው።
ይህንን መሠረት አድርጎ በተፈጠረ የአቋም ልዩነት ምክንያትም እነዚህ ሰዎችና ደጋፊዎቻቸው ዘርና ጎጥ ለይተው ከቤተ ክርስቲያኗ ተከፍለው በመውጣት ስላሴ ቤተ ክርስቲያንን በማቋቋም በወቅቱ ቤተ ክርስቲያንና ሕዝበ ክርስቲያኑ ለሁለት እንዲከፈል በማድረጉ ግንባር ቀደም ሚና የተጫወቱ ናቸው።
በእርግጥ መለያየቱና መከፋፈሉ የአቋም እንጂ የሃይማኖት ባለመሆኑ የሁለቱ ቤተ ክርስቲያናት አባላት ባላቸው የእምነት ጽናትና ቅንነት አንድ የሚያደርጋቸውን ሃይማኖታቸውንና ኢትዮጵያዊነታቸውን መሠረት በማድረግ በየበዓላቱ እየተገናኙ በሰላምና በመከባበር ይኖሩ ነበር።
ይህ ሰላምና መከባበር በእግዚአብሔር ፍቃድ ዘለቄታዊ አንድነትን ለማምጣት መሠረት ሊሆን ይችላል ተብሎ ሲታሰብ በአሁኑ ወቅት ግን ከዚህ ይልቅ በርዕሰ አድባራት ለንደን ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የተፈጠረን አስተዳደራዊ ችግር በማየት ምእነዚሁ ቤተ ክርስቲያኗን የከፈሉ ሰዎች አሁን ደግሞ ራሳቸውን ሃገረ ስብከት ብለው ባቋቋሙት የቻሪቲ ድርጅት አማካኝነት የርዕሰ አድባራት የንደን ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያንን የበላይ ባለሥልጣን በመሆን ቤተ ክርስቲያኗን በቁጥጥራቸው ሥር ለማዋል በመጣር ላይ መሆናቸውን ሁሉም ወገን ሊገነዘበው ይገባል።
UKም ሆነ በመላው ዓለም በስደት ላይ የምትኖሩ ኢትዮጵያውያን ሆይ፡
የወያኔ ኢህአዲግ ሥርዓት ሃገር ውስጥ ያለውን የኢኮኖሚ፤ የፓለቲካ፤ የዲፕሎማሲ፤ የወታደራዊ ሥልጣን ሁሉ በአንድ ጎሳ አባላት ቁጥጥር ሥር ማዋል አንሶት የተከበረው የኢትዮጵያ ኦርቶዶድስ ተወሕዶ ቤተ ክርስቲያንም እንዲሁ ከአናቱ ጀምሮ በአንድ ጎሳ ቁጥጥር ሥር እንዲውል እየተደረገ ለ20 ዓመት ከተዘለቀ በኋላ የነበሩትን ፓትርያርክ ሞት ሲወስዳቸው እንኳ ዘረኝነቱ ሳይለወጥ፤ እግዚአብሔርም ሳይፈራና ሕዝብም ሳይታፈር ዛሬም እንደገና የትግራይ ጎሳ ተፈልጎ በፓትርያርክነት እንዲሾም ተደርጓል።
ይህ ሁሉ አልበቃ ብሎ ነው ዛሬ ደግሞ በስደት ላይ የሚገኘው የኦርቶዶክስ እምነት ተከታይ ገንዘቡን፤ ጊዜውን፤ ጉልበቱንና እውቀቱን አስተባብሮ ቤተ ክርስቲያን አቁሞ እምነቱን ሲያራምድ አሁንም የሚያዝህ ወያኔ ኢህአዲግ ነው፤ ሹመኞቹም እንደ ሃገር ቤቱ ሁሉ ያው የትግሬው ጎሳ ናቸው በማለት በለንደንና በመላው አውሮፓን የሚገኙ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲይናትን ለመቆጣጠርና በመዳፍ ውስጥ ለማስገባት ደፋ ቀና የሚባለው ።
ስደተኛው በሚኖርበት እንደ UK ባለ ነፃነትና ፍትሕ በሰፈነበት ሃገር ወያኔ በሃገር ውስጥ የዘረጋውን የጎሳ አፓርታይድ ሥርዓት አምጥቶ በስደተኞች ቤተ ክርስቲያናት ውስጥ ማስፈን ከቻለ ስደተኛው ኢትዮጵያዊ ሕብረተ ሰብ ሳይሞት እንደሞተ ሊቆጥረው የሚገባ ሲሆን ነጻነትና ፍትሕ በሰፈነበት ሃገር የምንኖር ኢትዮጵያዊያን ወያኔ ከኢትዮጵያ አልፎ በስደት የምንኖርበት ድረስ መጥቶ መብታችንን ለመግፈፍ ሲሞክር መብትና ነጻነታችንን ማስከበር ሳንችል ከዚህ አልፈን በወያኔ መሣሪያና የወታደር ኃይል ታፍኖ ሥለሚገዛው የኢትዮጵያ ሕዝብ እጮሃለሁ ወይም እታገላለሁ ብሎ ማውራት ቀልድና ዘበት መሆኑን ልንረዳ ይገባናል።
በዚህ መሠረት በመላው UK፤ በአውሮፓና በመላው ዓለም የምንገኝ ስደተኛ ኢትዮጵያውያን ሁሉ ጥቃቅን ልዩነታችንን ወደ ጎን በመጣል ይህን የሃይማኖትና የስብዕና መብትን የማስከበር ትግልን ለጥቂት በቤተ ክርስቲያን አካባቢ ለሚንቀሳቀሱ ሰዎች ብቻ ሳንተው ሁላችንም ተነስተን በመረባረብ ወያኔን አይቀጡ ቅጣት ቀጥተን ነፃነታችንን በማስከበር ምሳሌነታችንን ማሳየት ይገባናል።
እግዚአብሔር አንድነታችንን ያጠንክርልን!! አሜን።

No comments:

Post a Comment