Wednesday, May 1, 2013

በኖርዌይ ያሉ ኢትዮጵያውያን ጩኸት ግን የእነርሱ ብቻ ጩኸት ሳይሆን በአለም ዙርያና በኢትዮጵያ ውስጥ ያሉትም ኢትዮጵያውያን ጩኸት ጭምር ነው


በኖርዌይ ኢትዮጵያዊያን ወገኖቸ ኮራሁ ለኢትዮጵያ የጉብኝት ዘመን ደረሰ ይሆን?
ዳንኤል፣ ከኖርዌይ
ይህንን ጽሁፍ እንድጽፍ ያነሳሳኝ april 28,2013 በኖርዌይ ዋና ከተማ ኦስሎ የወያኔ ተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ላይ ያየሁትና የሰማሁት የኢትዮጵያውያን ጩኸት ነው። በዚህ ሰላማዊEthiopians demonstration in Norway, Oslo ሰልፍ ላይ የወያኔ ግፍ ያንገፈገፋቸው ኢትዮጵያውያን ይጮሃሉ፥ኦሮሞው ይጮሃል፣ አማራው ይጮሃል፣ ጉራጌው ወዘተ ይጮሃል። ሴቱ ይጮሃል፣ወንዱ ይጮሃል ሙስሊሙ ይጮሃል፣ክርስቲያኑ ይጮሃል…. ኧረ የማይጮህ የለም ሁሉም ሰው ይጮሃል።
በኖርዌይ ያሉ ኢትዮጵያውያን ጩኸት ግን የእነርሱ ብቻ ጩኸት ሳይሆን በአለም ዙርያና በኢትዮጵያ ውስጥ ያሉትም ኢትዮጵያውያን ጩኸት ጭምር ነው። ከወያኔና ከደጋፊዎቻቸው ዉጭ ያሉ ኢትዮጵያውያን ጩኸት ነዉ።ግፍ በቃን፥ዘረኝነት በቃን፥አፓርታይድ በቃን፥ፉሺዝም በቃን የሚል ጩኸት፣ ከአንደበት ብቻ ሳይሆን ከልብ የሚወጣ ጩኸት።
ኢትዮጵያዊዉ በየበረሃው ይጮሃል፣በሲና በረሃ ሆዱ እየተቀደደ ሆድ ዕቃው እየወጣበት ይጮሃል፥ ወደስደት ሲነጉድ በየመንገዱ በአውሬ እየተበላ ይጮሃል፥የሚጓዝባት ጀልባ እየሰጠመች በሞት ጥላ መካከል ሆኖ ኢትዮጵያውያዊው ወገኔ ይጮሃል፣በተለያዩ ሃገራት እስር ቤቶች የታጎሩ ሴትና ወንድ ኢትዮጵያውያዊያን ይጮሃሉ።
በየአረብ አገራት ለዘመናዊ ባርነት ተሽጠው ከአሰሪዎቻቸው ግፍ የተነሳ በፈላ ዘይት እየተቃጠሉ ይጮሃሉ፣በአለንጋ እየተገረፉ ይጮሃሉ፣ ከፎቅ ላይ እየተወረወሩ ይጮሃሉ፣ የጉልበት ዋጋቸውን ተነጥቀው ይጮሃሉ፣ በወሮበሎች እየተደፈሩ ይጮሃሉ ሌሎቹም ህጋዊ ፈቃድ የላችሁም ተብለው እየተሳደዱ ይጮሃሉ፣
በኢትዮጵያ ውስጥ የዘር ማጥፉት ሰለባ የሆነው የአኙዋክ ወገኖቻችን ይጮሃሉ፣ አማራ ነህና በዚህ አትፈለግም ተብሎ በግፍ ከየስፍራው እየተሰደደ ያለው ወገኔ በየእስር ቤቱ የተጋዘው ኦሮሞ ወገኖቼ ይጮሃሉ፣ እውነትን በመጻፉቸውና በመናገራቸው ብቻ እስከሞት ድረስ የተፈረደባቸው ወገኖቼ ይጮሃሉ፣ በዋልድባ እየተገረፉና እየተሰደዱ ያሉ መነኮሳት ይጮሃሉ፣አብርሃና አቶ አስገደ ከትግራይ ይጮሃሉ ኧረ ዛሬማ የሚገርም ነገር ሰማሁ አባመላ የተባለ በዳያስፓራ ቀንደኛ የወያኔ ሰው ይጮሃል ሲባል።አሁንማ ማን የማይጮህ አለ? ሁሉንም የሚያስጮኸው ግን አንድ ነገር ነው፣የወያኔ ግፍ።
የኖርዌይ ኢትዮጵያዊያን ጬኸት የወያኔን ሹማምንትና ደጋፊዎች አዋርዶ እኛን ኢትዮጵያዊያንን አኩርቷል። እያሪኮን እንዳፈረሰው የእስራኤላዊያን ጩኸት ነበር።
ለእኔ ግን ለኢትዮጵያ የጉብኝት ዘመን ደረሰ ይሆን? የሚል ጥያቄ አስነሳብኝና የእስራኤላዊያን በግብፅ 400 ዓመት የባርነት ህይወት በኋላ የነፃነት ዘመን ሲደርስ የነበረው ሁኔታ ከአሁኑ የአገራችን ሁኔታ ጋር ተመሳስሎብኛልና ምስስሉን ከመፅሃፍ ቅዱስ እያጣቀስኩ ላሳይ፥
1. እግዚአብሄር ለአብርሃም የገባው የተስፉ ቃል-ዘርህ ለእርሱ ባልሆነች ምድር ስደተኞች እንዲሆኑ በእርግጥ እወቅ፤ ባሪያዎች አድርገውም አራት መቶ ዓመት ያስጨንቋቸዋል። ደግሞም በባርነት በሚገዙአቸው ሕዝብ ላይ እኔ እፈርዳለሁ፤ ከዚያም በኋላ በብዙ ከብት ይወጣሉ።(ዘፍጥረት 15፥13)
እግዚአብሄር ለኢትዮጵያ የገባው የተስፉ ቃል-ኢትዮጵያ እጆችዋን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች። (መዝሙር 68፥31)
2. የእስራኤላዊያን መከራ በግብፃውያን ገዢዎቻቸው-ግብፃውያንም የእስራኤልን ልጆች በመከራ ገዙአቸው። በጽኑ ሥራ፥ በጭቃ፥ በጡብም በእርሻም ሥራ ሁሉ፥ በመከራም በሚያሠሩአቸው ሥራ ሁሉ፥ ሕይወታቸውን ያስመርሩአቸው ነበር።(ዘፀአት1፥13-14)
የኢትዮጵያዊያን መከራ በወያኔ ገዢዎቻቸው-ወያኔዎችም የኢትዮጵያን ልጆች በመከራ ገዙአቸው። በጽኑ ዘረኝነት፥ በስደት፥ ከስፍራ በማፈናቀል ሁሉ፥ በእስር ሁሉ፥ ሕይወታቸውን ያስመርሩአቸው ነበር።
3. የእስራኤላዊያን ጩኸትና በእግዚአብሔር መደመጥ -ከዚያም ከብዙ ቀን በኋላ እንዲህ ሆነ፤ የግብፅ ንጉሥ ሞተ፤ የእስራኤልም ልጆች ከባርነት የተነሣ አለቀሱ፥ ጮኹም፥ ስለ ባርነታቸውም ጩኸታቸው ወደ እግዚአብሔር ወጣ።(ዘፀዓት 2፥23)
የኢትዮጵያዊያን ጩኸትና በእግዚአብሔር መደመጥ-ከዚያም21 አመት በኋላ እንዲህ ሆነ፤ የወያኔ ንጉሥ መለስ ሞተ፤ የኢትዮጵያ ልጆች ከባርነት የተነሣ አለቀሱ፥ ጮኹም።
4. እግዚአብሔርም የለቅሶአቸውን(የእስራኤላዊያንን) ድምፅ ሰማ፥ እግዚአብሔርም ከአብርሃምና ከይስሐቅ ከያዕቆብም ጋር ያደረገውን ቃል ኪዳን አሰበ።(ዘፀዓት 2፥24)
ታዲያ ወገኖቸ ይህ የኢትዮጵያዊያን ጩኸት በእግዚአብሄር ዘንድ ይሰማል የሚል እምነት አለኝ።ያን ጊዜ ደግሞ እንዲህ ይሆናል፣ እግዚአብሔርም የለቅሶአችንን ድምፅ ይሰማል፥ እግዚአብሔርም ከኢትዮጵያዊያን ጋር ያደረገውን ቃል ኪዳን ያስባል ።
የእስራኤላዊያንን ነፃነት የሰጠ እግዚአብሄር ለኢትዮጵያዊያንም ነፃነታችንን እንድንጎናፀፍ ይረዳናል። እኔ ለኢትዮጵያ የጉብኝት ዘመን እንደደረሰ አምናለሁ፥እስከዛው ጬኸታችንን እንቀጥል።
የኖርዌይ ኢትዮጵያዊያን በእናንተ ኮርቻለሁ፣በርቱ።
እግዚአብሄር ኢትዮጵያን ይባርክ!

No comments:

Post a Comment