Thursday, May 9, 2013

አቶ መለስን የሚመጥን ጥቅስ ፍለጋ፤ “ኢህአዴግን ነፍስ ይማርልን!”

zአንዳንድ ወዳጆቻችን ልክ በህይወት ያሉ እስኪ “መስል ድረሰ መለስ ለልደትህ እንኳን አደረሰህ!… መልካም የልደት በዓል ይሁንልህ!” ሲሏቸው አይቼ ሳቅቼ ሳቅቼ ሞተውት! (ደግሞ እኮ …አንተ… ነው የሚሏቸው …ወይ ጫማ መለካካት!)
እንደ እውነቱ ስለ መለስ የልደት ቀን መታሰቢያ ለማድረግ ከኔ የሚቀድም አካል መኖር አልነበረበትም፡፡ ያ ሁሉ ወዳጅነታችን ከግባ መሬቱ ጋር አብሮ የተቀበረ አስመሰልኩት እኮ!
“ስለ አቶ መለስ ልደት ስናወራ የሚመጥነውን ጥቅስ ማግኘት ይከብዳል!” አለ አንድ ዋነኛ የኢህአዴግ ካድሬ እውነት ብሏል ስለ መለስ ለማውራት ራሳቸው በተለያዩ የሞቅታ ቀናት የተነገሯቸው ንግግሮች ካልሆኑ በቀር የሚመጥናቸውን ጥቅስ ማግኘት ከባድ ነው፡፡
ከሞቅታት በአንዱ ቀን አቶ መለስ ዜናዊ አስረስ፤ እንዲህ ብለው የማይረሳ ንግግር ተናግረው ነበር፤ “በአንድ ድርጅት ውስጥ የአንድ ሰው ስብዕና መግዘፍ ከጀመረ ያ ድርጅት ሞቷል ማለት ነው” ኦ…. ብፃይ መለስ አፌ ቁርጥ ይበለልዎ!
በህይወት እያሉ እኛ የሀገራችንን መልካም ገፅታ ስንገነባ እርሳቸው ግን የራሳቸውን መልካም ገፅታ ሲገነቡ ነበር፡፡ እንዴት ያሉ የመልካም ገፅታ ግንበኛ መሰልዎት…! በስታድየም አካባቢ እንኳ ከሶስት በላይ ፖስተሮቻቸው ከኑሮ ውድነቱ በላይ ተሰቅለው ነበር፡፡ በየ ክፍለ ሀገሩ በየቀበሌው እና በየ ሰፈሩ ሳይቀር መለስ ያልተሰቀሉበት አልነበረም፡፡
አንዳንዶች “ይህንን መለስ አላዘዙም” ሲሉ ቢደመጥም እኛ ግን እናውቃለን ብንናገር እናልቃለን ብለን ፀጥ ብለን ቆይተናል፡፡
አንዳንድ ሰዎች የአቶ መለስን የህይወት ዘመን የስራ እንቅስቃሴ በአጭሩ ግለፁ ሲባሉ “…በተለይ ከሆነ ጊዜ ወዲህ እኛን በሳቅ ሲያፈርሱ፤ ራሳቸውን ደግሞ በምስል ሲገነቡ የኖሩ ታላቅ መሪ!” ይሏቸዋል፡፡
ሰሞኑን ደግሞ “አቶ መለስ የዋሉልን አንድ የማይረሳ ትልቅ ውለታ አለ” ሲል አንድ ወዳጄ ነገረኝ፤ ሁለመናዬን ጆሮ አድርጌ ምን ይሆን ወዳጄ… ብለው… “በጊዜ መሞታቸው” አለኝ!
አቶ መለስ ዜናዊ አሁን ሞተዋል፡፡ የገፅታ ግንባታቸው ግን አልሞተም፤
እውነትም አቶ መለስን ስናስብ ራሳቸው ከተናገሩት ውጪ ሌላ ጥቅስ ማግኘት ከባድ ነው፡፡ እስቲ እንድገማት፤ “በአንድ ድርጅት ውስጥ የአንድ ሰው ስብዕና ጎልቶ ከወጣ” ድርጅቱ ሞቷል ማለት ነው፡፡” ስለዚህ እንደ አቶ መለስ አነጋገር ኢህአዴግዬ የሞተችው ከእርሳቸውም ቀድማ ነው እናም ኢህአዴግ ሆይ… ነፍስ ይማርልን! ማለት አለብን ማለት ነው፡፡
በመጨረሻም፤
ከጥቂት ቀናት በኋላ አቶ መለስ “በአበበ ገላው ውርጂብኝ” የደነገጡበት ቀን ይከበራል፡፡ ስለዚህ መላው ወዳጆቻቸውን ለበዓለ ልደታቸው ብቻ ሳይሆን ለበዓለ ድንጋጤያቸውም እንኳን አደረሳችሁ! ለማለት እወዳለሁ!

No comments:

Post a Comment