Tuesday, May 21, 2013

የለንደን ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤ/ክ ጠቅላላ መንፈሳዊ ጉባኤ የአቋም መግለጫ

የለንደን ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤ/ክ ጠቅላላ መንፈሳዊ ጉባኤ የአቋም መግለጫ

london church
የርዕሰ አድባራት ለንደን ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ጠቅላላ መንፈሳዊ ጉባኤ የአቋም መግለጫ
ግንቦት ፲፩/ ፪ሺ፭ (19th May 2013)
የርዕሰ አድባራት ለንደን ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ጠቅላላ መንፈሳዊ ጉባኤ፤ ከእዚህ በፊት የቤተ ክርስቲያኗን አስተዳደር አቋም፣ የውስጥ መተዳደሪያ ደንብና ትረስት ዲድ በሚመለከት ያሳለፋቸው ውሳኔዎችና መግለጫዎች ሙሉ በሙሉ እንደተጠበቁ ሆነው፤ የቤተ ክርስቲያናችንን ችግር ለመፍታት በሚደረገው ጥረት ውስጥ የተከሰቱ፣ የተሳሳቱ መረጃዎችንና መግለጫዎችን ለማስተካከል፤ ጠቅላላ መንፈሳዊ ጉባኤው የሚከተለውን የአቋም መግለጫና ማብራሪያ አውጥቷል።
1)  የርዕሰ አድባራት ለንደን ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መንፈሳዊ ግንኙነቷ አዲስ አበባ ከሚገኘው ቅዱስ ሲኖዶስ ሲሆን፤ አስተዳደሯ ግን በቃለ ዓዋዲው፣ በ2006 ባወጣችው ደንብ፣ በተሻሻለው ትረስት ዲድና በእንግሊዝ ቻሪቲ ሕግ መሰረት (አስተዳዳሪን ጨምሮ) በምትመርጣቸው የሰበካ አስተዳደር ጉባኤ አባላት ወይም ባላደራዎችና ልዩ ልዩ ንኡንስ ኮሚቴዎች አማካኝነት/መሰረት ብቻ፤ ያለማንም የውጪ አካል ጣልቃ ገብነት ራሷን ችላ ትተዳደራለች። የቤተ ክርስተያኗም ንብረት አስተማማኝ በሆነ መንገድ ለመጪው ትውልድ ለማቆየት በሚያስችል መንገድ፤ የቤተ ክርስቲያኗ አባላት ብቻ በሚያጸድቁት ደንብ/ሕግ መሰረት ይያዛል፣ ይጠበቃል።
2)  የርዕሰ አድባራት ለንደን ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን የአስተዳደር መሰረቶች፤ በ2006 ዓ.ም. የጸደቀው፤ የውስጥ መተዳደሪያ ደንብ፣ ትረስት ዲድና ከእዚህ በፊት የጠቅላላ መንፈሳዊ ጉባኤው ያወጣቸው የአቋም መግለጫዎችና በእዚህ ሰነድ በተራ ቁጥር አራት ላይ በተጠቀሰው መሠረት ተሻሽለው፤ በጠቅላላ መንፈሳዊ ጉባኤው የሚጸድቁ የውስጥ መተዳደሪያ ደንቦች፣ የትረስት ዲድስ፣ የአቋም መግለጫዎችና ውሳኔዎች ብቻ ናቸው።
3)  የመንበረ ጵጵስና ሀገረ ሰብከትን በሚመለከት፤ ቤተ ክርስቲያኗ ከ2006 ዓ.ም ጀምሮ የምትመራበትና የምትተዳደርበት የውስጥ ደንብ በሚያዘውና ቤተ ክርስቲያኗ ባወጣችው የአቋም መግላጫ መሠረት በመሆኑ፤ አሁን ተቋቁሟል በተባለው “የሰሜን ምዕራብ አውሮፓ ሀገረ ስብከት” ውስጥ፤ የርዕሰ አድባራት ለንደን ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ምንም ዓይነት ተሳትፎና ግንኙነት ስለሌላት፤ ለሀገረ ስብከቱ እውቅና አትሰጥም። ለወደፊት ከሀገረ ስብከት ጋር የሚኖራት ግንኙነት የቤተ ክርስቲያኗ አባላት ተነጋግረው የሚወስኑት ጉዳይ ነው።
4)  የቤተ ክርስቲያኗ የውስጥ መተዳደሪያ ደንብና ትረስት ዲድ፤ ጠቅላላ መንፈሳዊ ጉባኤው በ 14/04/2013 ባሳለፈው ውሳኔ መሠረት፤ አሁን ባሉት አርቃቂ ኮሚቴ አስረጅነትና በተቋቋመው ገለልተኛ አወያይ ኮሚቴ መሪነትና ሊቀ መንበርነት፤ በአዲሱ የሰበካ አስተዳደር ጉባኤ አስተነባባሪነት፤ ተጠናቆ ሲጸድቅ ሌላ አዲስ የሰበካ አስተዳደር ጉባኤ (ባላደራዎች) ይመረጣል።
5)  አሁን በቤተ ክርስቲያናችን ውሰጥ የተከሰተው ችግር፤ የሃይማኖት/እምነት ችግር ሳይሆን የአስተዳደር ችግር ስለሆነ፤ ከላይ በተራ ቁጥር አንድ በተጠቀሰው መሠረት ለችግሩ መፍትሔ የሚሰጡት የቤተ ክርስቲያኗ አባላት ብቻ ስለሆኑ፤ ቅዱስ ሲኖዶሱም ሆነ ቤተ ክርስቲያኗ እውቅና የማትሰጠው “ሀገረ ስብከት” ችግሩን ለአባላቶች በመተው የቤተ ክርስቲያኗ አባላት በውስጥ ደንባችንና በእንግሊዝ ሀገር የቻሪቲ ሕግ መሠረት እንድንፈታው ይሆን ዘንድ በትህትና እያሳሰብን፤ ጸሎታቸውና ቡራኬአቸው ግን እንዳይለየን እንጠይቃለን።
6)  ከላይ በተጠቀሰው መሠረት የቤተ ክርስቲያናችን ችግር የሚፈታው በአባላቷ ብቻ ስለሆነ፤ የሌሎች አብያተ ክርስቲያናት አባላት (የቅድስት ሥላሴ፣ የቅዱስ ገብረኤልና የጸራጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያንና የሌሎች በለንደንና አካባቢው የሚገኙ የአብያተ ክርስቲያናት አባላት) በቤተ ክርስቲያናችን የውስጥ ጉዳይ ጣልቃ እንዳይገቡብን ከታላቅ አክብሮት ጋር አበክረን እናሳስባለን። ይህ በአንድ አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን ጉዳይ ውስጥ የሌላ አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን ጣልቃ ገብነት፤ በክርስቲያኖች መካከል ከፍተኛ አለመግባባትና ከፍተኛ ቅራኔን የሚጭር ከመሆኑም በላይ፤ በሕገ ቤተ ክርስቲያንም ሆነ በእንግሊዝ ሀገር የቻሪቲ ሕግ ተቀባይነት የሌለው ሕገ ወጥ ተግባር እንደሆነ ለማስገንዘብ እንወዳለን።
7)  በለንደንና አካባቢዋ ያሉ ካህናት፤ ሰሞኑን ከአዲስ አበባ ለመጡ ሁለት ሊቃነ ጳጳሳት የአቋም መግለጫ በማውጣት ፈርመው መስጠታቸውን ለማወቅ ተችሏል። ይህ የካህናቱ መግለጫም ሆነ አቋም ግን የርዕሰ አድባራት ለንደን ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያንን ካህናትና ምዕመናን የማይመለከትና ተቀባይነትም የሌለው መሆኑን አጥብቀን እናሳውቃለን።
8)  በተራ ቁጥር 7 ላይ የተጠቀሰውን መግለጫ፤ የተወሰኑ የለንደን ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን አገልጋይ ወይም አገልጋይ የነበሩ ካህናት ተሰማምተው መፈረማቸውን ለማወቅ የተቻለ ሲሆን፤ ይህንን ግን ጠቅላላ መንፈሳዊ ጉባኤው የማይደግፈውና የማይቀበለው ሲሆን፤ ካህናቱም ተስማምተው የፈረሙት በግል ስማቸው ብቻ እንጂ የርዕሰ አድባራት ለንደን ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያምን ካህናትና ምዕመናን ወክለው አለመሆኑን አጥብቀን እናስገነዝባለን።
9)  በቀድሞው የለንደን ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ ቆሞስ አባ ግርማ ከበደና፤ በጥቂት የቀድሞው የሰበካ አስተዳደር ጉባኤ አባላት አማካይነት፤ ከሌሎች ደብሮች ጋር በመተባበርም ሆነ በግል የሚወጡ የአቋም መግለጫዎችም ሆነ ምርጫዎች፤ የርዕሰ አድባራት ለንደን ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ጠቅላላ መንፈሳዊ ጉባኤ የማይደግፈውና የማይቀበለው ከመሆኑም በላይ ሕጋዊነት የሌለው መሆኑን አጥብቀን እናሳውቃለን።
10) የርዕሰ አድባራት ለንደን ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ጠቅላላ መንፈሳዊ ጉባኤ፤ በ21/04/2013 ባደረገው ስብሰባ ላይ 9 አባላት ያሉት አዲስ የሰበካ አስተዳደር ጉባኤ አባላቶች/ባላደራዎች መምረጡ ይታወሳል። ይህ አዲስ የሰበካ አስተዳደር ጉባኤ የስራ ሃላፊነቱን ከቀድሞው የሰበካ አስተዳደር ጉባኤ መረከብ ይችል ዘንድ የተጀመረው የሕግ እንቅስቃሴ እንዲቀጥልና የቻሪቲ ኮሚሽን ባዘዘው መሰረት ተወካዮቻችን፤ በተጀመረው የሚዲዬሽን(Mediation) ስራ መሠረት ጉዳዩ ተፈፃሚነት እንዲያገኝ፤ ይህ ካልሆነም በቻሪቲ ኮሚሽንም ሆነ በፍርድ ቤት በኩል የአባላትን መብት ለማስከበር የሚደረገውን እንቅስቃሴ ሙሉ በሙሉ ይህ ጉባኤ እንደሚደግፈው እንደገና ለማረጋገጥ እንወዳለን።
ወስብሐት ለእግዚአብሔር!

No comments:

Post a Comment